1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የመጋቢት 30 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ መጋቢት 30 2016

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ትናንት በፈረንሳይ ፓሪስ ማራቶን በወንድም በሴትም ድል ተቀዳጅተዋል ። ከወሳኙ ድል በኋላ አትሌቶቹን አነጋግረናል ። በአውሮጳ ሻምፒዮንስ ሊግ የሩብ ፍጻሜ ፍልሚያዎች ነገና ከነገ በስትያ ይከናወናሉ ። በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ሊቨርፑል በተከላካይ ብርቱ ስህተት ድሉን አሳልፎ ሰጥቷል ። ባየር ሙይንሽንን ዘንድሮ ምን ነካው?

https://p.dw.com/p/4eXIM
Bundesliga | 1. FC Heidenheim - Bayern München
ምስል Tom Weller/dpa/picture alliance

ሣምንታዊ የስፖርት ዘገባ

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ትናንት በፈረንሳይ ፓሪስ ማራቶን በወንድም በሴትም ድል ተቀዳጅተዋል ። ከወሳኙ ድል በኋላ አትሌቶቹን አነጋግረናል ። በአውሮጳ ሻምፒዮንስ ሊግ የሩብ ፍጻሜ ፍልሚያዎች ነገ እና ከነገ በስትያ ይከናወናሉ ። ለሩብ ፍጻሜ ከደረሱት ውስጥ ሦስቱ የስፔን ቡድኖች ናቸው ። የጀርመን እና እንግሊዝ ሁለት ሁለት ቡድኖችም ለሩብ ፍጻሜው ከደረሱት ውስጥ ይገኛሉ ። ፈረንሳይ ወደ ግማሽ ፍጻሜ የማለፍ ተስፋዋ በአንድ ቡድን ብቻ ተወስኗል ። ባየር ሙይንሽንን ምን ነካው? ከታችኛው ዲቪዚዮን ዘንድሮ ወደ ቡንደስሊጋው በመጣው ቡድን ተሸንፎ የደጋፊዎቹን አንገት አሰብሯል ። ሽንፈቱ ለባዬር ሌቨርኩሰን የዋንጫ ግስጋሴ መልካም ዕድል ፈጥሯል ። በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ሊቨርፑል በተከላካይ ብርቱ ስህተት ድሉን አሳልፎ ሰጥቷል ።

በፕሬሚየር ሊግ ሊቨርፑል መሪነቱን ከእጁ አስወጥቷል 

በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ኦልድ ትራፎርድ ትናንት በደጋፊዎች ስትናጥ አምሽታለች ።  ሊቨርፑል በሉዊስ ዲያዝ 23ኛ ደቂቃ ላይ በተቆጠረ ግብ ሲመራ ቆይቶ ነበር የመጀመሪያ አጋማሽ የተጠናቀቀው ። እንደ አያያዙ ከሆነ ብዙዎች የትናንቱን ጨዋታ ሊቨርፑል አሸንፎ ከአርሰናል በ2 ነጥብ ርቀት በዋንጫ ግስጋሴው ይገፋበታል ብለው ገምተው ነበር ። ከረፍት መልስ ግን በተከላካዩ ብርቱ ስህተት ሊቨርፑል ይህን የማሸነፍ እድሉ ከእጁ አፈትልኮ ወጥቷል ። 

50ኛው ደቂቃ ላይ ብሩኖ ፈርናንዴሽ ድንገት የሊቨርፑል ደጋፊዎችን ልብ ቀጥ አድርጓል ። ኳንሳስ ለመሀል ተከላካዩ ቫን ዳይክ በተልመሸመሸ መልኩ አቀብላለው ያለው ኳስ በቀጥታ ያረፈው አድብቶ ሲጠብቅ የነበረው ብሩኖ እግር ላይ ነበር ። የግብ ጠባቂው ከግብ ክሉ ውጪ መሆኑን የተመለከተው ብሩኖ ፈርናንዴሽ ግብ ጠባቂውን አንጠራርቶ በድንቅ ሁኔታ ኳሷን ከመረብ በማሳረፍ የሊቨርፑል የድል ግስጋሴ ላይ ቀዝቃዛ ውኃ ቸልሷል ።

እንደውም 67ኛው ደቂቃ ላይ በኮቢ ማይኖ ግሩም ግብ መሪነቱን የጨበጠው ማንቸስተር ዩናይትድ ሊቨርፑሎችን አስጨንቆ ቆይቷል ። ብዙም በመከላከሉ ላይ በማተኮሩም በደረሰበት ጫና የተገኘችውን ፍጹም ቅጣት ምት ሞሀመድ ሳላኅ 84ኛው ደቂቃ ላይ ግብ ጠባቂውን በተቃራኒ አቅጣጫ በመላክ አቻ የምታደርገውን ግብ አስቆጥሯል ። የመጋቢት 23 ቀን 2016 የስፖርት መሰናዶ

ሞሀመድ ሳላኅ ሊቨርፑልን አቻ የምታደርገውን ግብ ካስቆጠረ በኋላ
ሞሀመድ ሳላኅ 84ኛው ደቂቃ ላይ ግብ ጠባቂውን በተቃራኒ አቅጣጫ በመላክ ሊቨርፑልን አቻ የምታደርገውን ግብ በፍጹም ቅጣት ምት ካስቆጠረ በኋላምስል Dave Thompson/AP/picture alliance

በዚህም መሠረት፦ ባለፈው ግጥሚያ ከማንቸስተር ሲቲ ጋ ያለምንም ግብ የተለያየው አርሰናል ከሊቨርፑል እኩል 71 ነጥብ ሰብስቦ በግብ ክፍያ ልዩነት የፕሬሚየር ሊጉ መሪነቱን ተረክቧል ።  ማንቸስተር ሲቲ በ70 ነጥብ ሦስተኛ ነው ። ሉቶን ታወን፤ በርንሌይ እና ሼፊልድ ዩናይትድ ከ18ኛ እስከ 20 ደረጃ ወራጅ ቀጣናው ውስጥ ይገኛሉ ።

በ60 ነጥብ 4ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ቶትንሀም ሆትስፐር ትናንት ኖቲንግሀም ፎረስትን 3 ለ1 ድል አድርጓል ። ቸልሲ ከሼፊልድ ዩናይትድ ጋ ሁለት እኩል ተለያይቷል ። ቅዳሜ ዕለት አርሰናል ብራይተንን 3 ለ0 ድል ሲያደርግ፤ ማንቸስተር ሲቲ ክሪስታል ፓላስን 4 ለ2 አሸንፏል ። ሉቶን ታወን በርመስን እንዲሁም ዌስትሀም ዩናይትድ ዎልቭስን 2 ለ1፤ ኒውካስል ፉልሀምን እንዲሁም ኤቨርተን በርንሌይን 1 ለ0 አሸንፈዋል ። አስቶን ቪላ ከብሬንትፎርድ ጋ ሦስት እኩል ተለያይቷል ።

በቡንደስሊጋው ባዬርን ሙይንሽን ምን ነካው?

በጀርመን ቡንደስ ሊጋ የበርካታ ጊዜያት የዋንጫ ባለድሉ ባዬርን ሙይንሽን ዘንድሮ ከታችናው ዲቪዚዮን ባደገው ሐይደንሀይም ቡድን መሸነፉ በርካቶችን አስደምሟል ። 2 ለ0 ሲመራ ቆይቶ የማታ ማታ የ3 ለ2 ሽንፈትን ያስተናገደው ባዬርን ሙይንሽን አሰልጣንኝ ቶማስ ቱኁል ጉዳይም አጠያያቂ ሆኗል ። አሰልጣኙ ከባዬርን ሙይንሽን መሰናበታቸው የማይቀር መሆኑ ቀደም ሲል ተነግሯል ። አሁን እስከ ዘንድሮ የቡንደስ ሊጋ ፍጻሜ ድረስስ ይቆያሉ ወይ የሚል ጥያቄ አጭሯል ።

የባዬርን ሙይንሽን አሰልጣንኝ ቶማስ ቱኁል ጉዳይ አጠያያቂ ሆኗል
ሽንፈት የደጋገሙት የባዬርን ሙይንሽን አሰልጣንኝ ቶማስ ቱኁል ጉዳይ አጠያያቂ ሆኗልምስል Tom Weller/dpa/picture alliance

ቅዳሜ ዕለት ዑኒዮን ቤርሊንን 1 ለ0 ያሸነፈው ባዬርን ሌቨርኩሰን አሁን በ76 ነጥብ የቡንደስ ሊጋው የደረጃ ሰንጠረዥ ቁንጮ ላይ ሰፍሯል ። ባዬርን ሙይንሽን በ16 ነጥብ ተበልጦ ሁለተኛ ነው ። ተመሳሳይ 60 ነጥብ ሰብስቦ በግብ ክፍያ ብቻ በመበለጥ 3ና ደረጃ ላይ የሚገኘው ሽቱትጋርት ቦሩስያ ዶርትሙንድን 1 ለ0 አሸንፏል ። እንደ ቦሩስያ ዶርትሙንድ 53 ነጥብ ሰብስቦ በግብ ክፍያ ግን 4ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ላይፕትሲሽ ፍራይቡርግን በገዛ ሜዳው 4 ለ1 ኩም አድርጓል ። ቮልፍስቡርግ ትናንት በቦሩስያ ሞይንሽንግላድባኅ የ3 ለ1 ሽንፈት አስተናግዷል ። ኮሎኝ ቦሁምን 2 ለ1 ሲያሸንፍ፤ ማይንትስ ዳርምሽታድትን 4 ለ0 ጉድ አድርጓል ። አይንትራኅት ፍራንክፉርት ከቬርደር ብሬመንን አንድ እኩል ተለያይቷል ። ማይንትስ ወራጅ ቃጣና ጠርዝ ላይ፤ ኮሎኝ እና ዳርምሽታድት 17ኛ እና 18ኛ ቁልቁል ይገኛሉ ። የመጋቢት 16 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በወንድም በሴትም ድል የተቀዳጁበት የፓሪስ ማራቶን   

አድማጮች፦ ወደ ሻምፒዮንስ ሊግ ትንታኔ ከማለፋችን በፊት ደግሞ የአትሌቲክስ ድል ዘገባ እናስደምጣችሁ ። ትናንት በፈረንሳይ ዋና ከተማ በተከናወነው የፓሪስ ማራቶን ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በወንድም በሴትም ድል ተቀዳጅተዋል። በወንዶች ፉክክር ሙሉጌታ ዑሙ (2:05:33) 1ኛ ወጥቷል ። በሴቶች ፉክክር ደግሞ መስታወት ፍቅር (2:20:45) እና እናት ጥሩሰው (2:20:48) 1ኛ እና 2ኛ ወጥተዋል ። ውድድሩን በስፍራው ተገኝታ የተከታተለችው የፓሪስ ዘጋቢያችን ሐይማኖት ጥሩነህ ለድል የበቁት አትሌቶቻችን አነጋግራለች ።

በወንዶች ፉክክር ሙሉጌታ ዑሙ (2:05:33) 1ኛ ወጥቷል
በወንዶች ፉክክር ሙሉጌታ ዑሙ (2:05:33) 1ኛ ወጥቷልምስል Haimanot Tiruneh/DW

የማራቶን ሩጫ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች

ከፓሪስ ማራቶን ድል ባሻገር፦ ኢትዮጵያውያንአትሌቶች በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች በተከናወኑ የአትሌቲክስ ፉክክሮች ድል ተቀዳጅተዋል ። በደቡብ ኮሪያ ዳጉ ማራቶን በሴቶች ፉክክር ኢትዮጵዊቷ አትሌት ሩቲ አጋ (2:21:08) 1ኛ ወጥታለች ። በወንዶች ኬንያውያን አሸንፈዋል ። በጣሊያን ሚላኖ ማራቶንም በሴቶች ፉክክር ኢትዮጵውያኑ አትሌቶች ትእግስት ዓለሙ (2:26:32) እና ፋንቱ ሹጊ (2:30:52) 1ኛ እና 3ኛ በመግባት ድል ተቀዳጅተዋል ።  በዚህም ፉክክር በወንዶች ኬንያውያን አሸንፈዋል ።  አውስትራሊያ ውስጥ በተኪያሄደው የሊንዝ ማራቶን ኢትዮጵያዊው አትሌት ደጀኔ ደበላ (2:08:33) 3ና ደረጃ ሲያገኝ፤ የኤርትራው ሯጭ ጎይቶም ክፍሌ (2:08:11) 1ኛ ወጥቷል ።  የ2ኛ ደረጃውን ኬኒያዊው አትሌት ዴኒስ ኪፕንጌኖ (2:08:24) አግኝቷል ።  ኬንያውያን ባሸነፉበት በዚሁ ውድድር በሴቶች ዘርፍ፦ ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ጉሉሜ ተክሌ (2:34:08) 3ኛ ወጥታለች ። 

የግማሽ ማራቶን ሩጫ ውጤቶች

በግማሽ ማራቶን ፉክክሮችም በተለይ በሴቶች ዘርፍ ኢትዮጵያውያን ድል ተቀዳጅተዋል ። ጀርመን ውስጥ በተከናወነው ፈጣኑ የቤርሊን ግማሽ ማራቶን ፉክክር ለጀርመን የምትሮጠው ትውልደ ኢትዮጵያ ጀርመናዊቷ አትሌት ሜላት ቀጀልቻ ( 1:07:26) በመሮጥ 3ኛ ወጥታለች ። በዚህ ውድድር ኢትዮጵያውያቱ አትሌቶች ሙሉዋት ተክሌ (66:53) በመሮጥ 1ኛ፤ ዘራይ ፍታዊ ደግሞ (67:22) 2ኛ ደረጃ አግኝተዋል ። በቼክ ሪፐብሊኩ የፕራኅ ግማሽ ማራቶን በሴቶች ፉክክር ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ጌጤ ዓለማየሁ (1:08:10) ሮጣ በማጠናቀቅ 1ኛ ወጥታለች ። ሌላኛዋ ኢትዮጵያዊት አትሌት ንግሥት ሐፍቱ (1:09:30) በመሮች የ3ኛ ደረጃ አግኝታለች ። በወንዶቹ ድሉ የ,ኬንያውያን ሆኗል ። በስፔን ማድሪድ ፉክክርም በሴቶች ኢትዮጵያዊቷ አበራሽ ሽሊማ (1:08:31) አሸንፋለች ። በወንዶች የኬንያ እና ኡጋንዳ አትሌቶች ተከታትለው በመግባት ለድል በቅተዋል ። በቻይና የሆሊ ሲቲ ግማሽ ማራቶን (1:10:17) ሮጣ ያጠናቀቀችው ኢትዮጵያዊቷ አትሌት  ብርሃን ገ7ጊዮርጊስ 3ኛ ደረጃ አግኝታለች ።  የመጋቢት 9 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የአውሮጳ ሻምፒዮንስ ሊግ ተጋጣሚ ቡድኖችን ለመለየት ጣ ሲወጣ ። ፎቶ፦ ከክምችት ማኅደር
የአውሮጳ ሻምፒዮንስ ሊግ ተጋጣሚ ቡድኖችን ለመለየት ጣ ሲወጣ ። ፎቶ፦ ከክምችት ማኅደርምስል Martial Trezzini/KEYSTONE/dpa/picture alliance

የሻምፒዮንስ ሊግ የሩብ ፍጻሜ ግጥሚያዎች

በሻምፒዮንስ ሊግ ወደ ግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ ነገ እና ከነገ በስትያ አራት ፍልሚያዎች ይኖራሉ ። ማክሰኞ ሚያዝያ 1 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፔኑ ሪያል ማድሪድ ከእንግሊዙ ማንቸስተር ሲቲ ጋ ይጋጠማል ። በተመሳሳይ ከምሽቱ አራት ሰአት ላይ ሌላኛው የእንግሊዝ ቡድን አርሰናል የጀርመኑ ባዬር ሙይንሽንን ይፋለማል ።  በነጋታው ረቡዕ ማታም በተመሳሳይ ሰአት ሁለት ጨዋታዎች ይኖራሉ ። የፈረንሳዩ ፓሪ ሳን ጃርሞ የስፔኑ ባርሴሎናንን ያስተናግዳል ።  የጀርመኑ ቦሩስያ ዶርትሙንድ በስፔኑ አትሌቲኮ ማድሪድ ኤስታዲዮ ሜትሮፖሊታኖ ስታዲየም ይፋለማል ። 

ወደ ሩብ ፍጻሜ ለማለፍ በነበሩ ግጥሚያዎች እንደ አትሌቲኮ ማድሪድ አሰልጣኝነታቸው ለ100ኛ ጊዜ ብቅ ያሉት ዲዬጎ ሲሞኔ በሩብ ፍጻሜው የመጀመሪያ ግጥሚያ ተጨማሪ ታሪክ ለማስመዝገብ ተዘጋጅተዋል ። የ53 ዓመቱ አሰልጣኝ እስካሁን 49 ውድድሮች ላይ ድል አስመዝግበዋል ። ረቡዕ ከተሳካላቸው 50ኛ ድላቸው ሆኖ ይመዘገባል ። የመጋቢት 2 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የሪያል ማድሪድ አሰልጣኝ የ64 ዓመቱ ካርሎ አንቼሎቲ
የሪያል ማድሪድ አሰልጣኝ የ64 ዓመቱ ካርሎ አንቼሎቲ ምስል Adam Davy/PA Wire/dpa/picture alliance

ከ50 በላይ ድሎችን ማስመዝገብ የቻሉ አሰልጣኞች

 እስካሁን ከ50 በላይ ድሎችን ማስመዝገብ የቻሉ አሰልጣኞች ስምንት ናቸው ። ካርሎ አንቼሎቲ ላይ የተጠጉት የቸልሲው አሰልጣኝ ፔፕ ጓርዲዮላ ናቸው ። እስካሁን 109 ጊዜ አሸንፈዋል ። የሪያል ማድሪድ አሰልጣኝ የ64 ዓመቱ ካርሎ አንቼሎቲ 114 ድሎችን በማስመዝገብ ቀዳሚ ናቸው ። የማንቸስተር ዩናይትድ የረዥም ዘመን አሰልጣኝ የ82 ዓመቱ ጡረተኛ ሠር አሌክስ ፈርግሰን በ102 ድሎች 3ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ ። አርሰናልን ለረዥም ዘመን ያሰለጠኑት ሌላኛው የ74 ዓመት ጡረተኛ አርሰን ቬንገር  82 ጊዜ አሸንፈዋል ። የኤኤስ ሮማ አሰልጣኝ የ61 ዓመቱ ሆዜ ሞሪኞ 77 ጊዜ በማሸነፍ አርሰን ቬንገርን ተከትለው 5ኛ ደረጃ ላይ ሠፍረዋል ። የ72 ዓመቱ የኔዘርላንድ ብሔራዊ ቡድን የቀድሞ አሰልጣኝ ሉዊ ቫንጋል በ95 ጨዋታዎች 57 ጊዜ ድል በመቀዳጀት 6ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ ። የ56 ዓመቱ የሊቨርፑል አሰልጣኝ ዬርገን ክሎፕ እስካሁን በ100 ጨዋታዎች 56 ጊዜ በማሸነፍ 7ኛ ደረጃውን ተቆናጠዋል ። ዘንድሮ በፕሬሚየር ሊጉ ዋንጫ የማንሳት እድላቸው ከፍተኛ ከሆኑ ሦስት አሰልጣኞች መካከልም ይገኛሉ ። የ63 ዓመቱ የቀድሞ የሊቨርፑል ሌላኛው አሰልጣኝ ራፋኤል ቤኒቴዝ በበኩላቸው በ95 ጨዋታዎች 53 ጊዜ ማሸነፍ ችለዋል ።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ሸዋዬ ለገሰ