1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የመጋቢት 9 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ መጋቢት 9 2016

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች እንደተለመደው በተለያዩ ዓለምአቀፍ የአትሌቲክስ ፉክክሮች ድል ተቀዳጅተዋል ። ግብጽ በበላይነት በምትመራው የአፍሪቃ ጨዋታዎች ምሽቱን ኢትዮጵያ ሁለት ወሳኝ ፉክክሮች ይጠብቋታል ። እጅግ አጓጊ በነበረው የእንግሊዝ ኤፍ ኤ ካፕ የሩብ ፍጻሜ ፍልሚያ ትናንት ቸልሲ በባከነ ሰአት ለድል በቅቷል ።

https://p.dw.com/p/4drsj
Champions League | Bayern München - Lazio
ምስል Angelika Warmuth/REUTERS

ሣምንታዊ የስፖርት ዘገባ

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች እንደተለመደው በተለያዩ ዓለምአቀፍ የአትሌቲክስ ፉክክሮች ድል ተቀዳጅተዋል ። ግብጽ በበላይነት በምትመራው የአፍሪቃ ጨዋታዎች ምሽቱን ኢትዮጵያ ሁለት ወሳኝ ፉክክሮች ይጠብቋታል ። እጅግ አጓጊ በነበረው የእንግሊዝ ኤፍ ኤ ካፕ የሩብ ፍጻሜ ፍልሚያ ትናንት ቸልሲ በባከነ ሰአት ለድል በቅቷል ። ሊቨርፑል በመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች የበላይነቱን አሳልፎ ሰጥቷል ።

አትሌቲክስ

ደቡብ ኮሪያ ውስጥ እናንት እሁድ በተካሔደው የሴዑል የማራቶን ሩጫ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በወንድም በሴትም ድል ተቀዳጁ ።  ብርቱ ፉክክር በታየበት የወንዶቹ የማራቶን ሩጫ አትሌት ጀማል ይመር በአንደኛነት ሲያሸንፍ፤ በሴቶች ደግሞ አትሌት ፍቅርተ ወረታ ለድል በቅታለች ።  አትሌት ጀማል ይመር ውድድሩን በአንደኛነት ለማጠናቀቅ የፈጀበት፦ 2 ሰዓት ከ06 ደቂቃ ከ08 ሰከንድ ነው ። ኬንያውያኑ ሮንዛስ ሎኪታም ኪሊሞ እና ኢድዊን ኪፕሮፕ ኪፕቶ ከጀማል በአንድ እና ሁለት ሰከንዶች ብቻ ተበልጠው ሁለተኛ እና ሦስተኛ ወጥተዋል።

በሴቶች ፉክክር ደግሞ ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ፍቅርተ ወረታ 2 ሰዓት ከ21 ደቂቃ ከ32 ሰከንድ በመሮጥ አንደኛ ወጥታለች ። ትውልደ ኢትዮጵያዊቷ የባሕሬን አትሌት ደሲ ጂሳ መኮንን ከ47 ሰከንዶች በኋላ ተከትላ በመግባት የሁለተኛ ደረጃ አግኝታለች ። በፍቅርተ በ1 ደቂቃ ከ20 ሰከንዶች የተበለጠችው ኬንያዊቷ ቪዝሊን ጄፕኬሾ ሦስተኛ ደረጃ በማግኘት አጠናቃለች ።

ስፔን ላሬዶ ውስጥ ቅዳሜ ዕለት በተካሔደው የ10 ሺሜትር የሩጫ ፉክክር የቤት ውስጥ ፉክክር ክብረወሰን ባለቤቱ ኢትዮጵያዊው አትሌት ዮሚፍ ቀጀልቻ 26.36 በመሮጥ  አሸንፏል ።   ዩጋንዳዊው ጆሽዋ ቼፕቴጊ እና ኢትዮጵያዊው አዲሱ ይሁኔ ሁለተኛ እና ሦስተኛ ወጥተዋል ። የመጋቢት 2 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

በሴቶች ተመሳሳይ ርቀት ፉክክር ጀርመናዊቷ ኮንስታንስ ክሎስተርሐልፈን 31:07 በመሮጥ አንደኛ ወጥታለች ።  ኬንያዊቷ ፒዩሪ ጊቶንጋ እና ስፔናዊቷ ኢርኔ ሳንቼዝ ኤስክሪባኖ ሁለተኛ እና ሦስተኛ ደረጃን አግኝተዋል ።

ከአትሌቲክስ ፉክክሩ ብዙ ይጠበቃል
የኢትዮጵያ ቡድን 62 ወንዶች እና 75 ሴቶች በድምሩ 137 አትሌቶችን አካቷል ።  በሩጫ ፉክክር 89 ወንዶች እና ሴቶች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ይሳተፉበታል ።ምስል Sven Hoppe/dpa/picture alliance

የአፍሪቃ ጨዋታዎች በጋና

ሁለተኛ ሳምንቱን ባስቆጠረው እና የተለያዩ የስፖርት ዘርፎችን በሚያካትተው የአፍሪቃ ጨዋታዎች ግብጽ አሁንም በበላይነት ትመራለች ። ግብጽ እስካሁን 91 የወርቅ፤ 35 የብር እና 30 የነሐስ በድምሩ 156 ሜዳሊያዎችን በመሰብሰብ አሁንም የመሪነቱን ስፍራ ተቆናጣለች ። ናይጄሪያ 27 የወርቅ፤ 21 የብር እንዲሁም 30 የነሐስ በድምሩ 78 ሜዳሊያዎችን ሰብስባ የሁለተኛ ደረጃ ይዛለች ። ደቡብ አፍሪቃ በ25 የወርቅ፤ በ29 የብር እና በ38 የነሐስ በድምሩ 92 ሜዳሊያ የሦስተኛ ደረጃ ላይ ትገናለች ። እንደ ደቡብ አፍሪቃ ካለፈው ሳምንት ደረጃዋ በአንድ ዝቅ ያለው አልጄሪያ በ22 የወርቅ፤ በ30 የብር እና በ37 የነሐስ በድምሩ 89 ሜዳሊያዎች አራተኛ ደረጃ ላይ ሰፍራለች ።

የኤርትራ ቡድን 6 የወርቅ፤ 2 የብር እና 5 የነሐስ በድምሩ 13ሜዳሊያዎችን ሰብስቦ ከአንድ እስከ ዐሥር ካሉት ሃገራት ተርታ በመሰለፍ 8ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ።

እስካሁን 1 የብር ሜዳሊያ ያገኘው የኢትዮጵያ ቡድን 26ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ።  የብር ሜዳሊያው የተገኘው በወንዶች የብስክሌት ፉክክር በኪያ ጀማል ባለፈው ዐርብ ነው ። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድን እጅግ በሚጠበቅበት የሩጫ ፉክክር ተሳታፊ የሁኑ አትሌቶች በሁለተኛ ዙር ትናንት አክራ ጋና ገብተዋል ።

ጋና አክራ በሚካሄደው የአፍሪቃ ጨዋታዎች ቡጢን ጨምሮ በ23 የስፖርት ዘርፎች ግጥሚያዎች ይኖራሉ
ጋና አክራ በሚካሄደው የአፍሪቃ ጨዋታዎች እግር ኳስ፤ የእጅ ኳስ፤ ነጻ ትግል፤ ባድሜንተን፤ የውኃ ዋና፤ ጁዶ፤ ቴኳንዶ፤ ብስክሌት፤ ቴኒስና ቡጢን ጨምሮ በ23 የስፖርት ዘርፎች ግጥሚያዎች ይኖራሉ ።  ምስል Sergiy Tryapitsyn/PantherMedia/IMAGO

ከዛሬ እስከ ዐርብ ድረስ በተከታታይ በተለያዩ ርቀቶች የሩጫ ፉክክሮች ይኖራሉ ። የ3000 ሜትር የወንዶች መሰናከል፤ የሴቶች 5000 ሜትር የፍጻሜ ውድድሮች ምሽቱን ይከናወናሉ ። በኢትዮጵያውያን አትሌቶች ውጤት የሜዳሊያ ሰንጠረዥ ፈጣን ለውጥ ይኖራል ተብሎ ይጠበቃል ። የኢትዮጵያ ቡድን 62 ወንዶች እና 75 ሴቶች በድምሩ 137 አትሌቶችን አካቷል ።  በሩጫ ፉክክር 89 ወንዶች እና ሴቶች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ይሳተፉበታል ።

የፊታችን ቅዳሜ በሚጠናቀቀው የአፍሪቃ ጨዋታዎች፦ እግር ኳስ፤ የእጅ ኳስ፤ ነጻ ትግል፤ ባድሜንተን፤ የውኃ ዋና፤ ጁዶ፤ ቴኳንዶ፤ ብስክሌት፤ ቴኒስን ጨምሮ በ23 የስፖርት ዘርፎች ግጥሚያዎች ይኖራሉ ።  

ኤፍኤ ካፕ

በትናንቱ የእንግሊዝ ኤፍ ኤ ካፕ የሩብ ፍጻሜ ፍልሚያ ማንቸስተር ዩናይትድ የማሸነፍ መንፈሱን አነቃቅቷል ። ዐራት ዋንጫዎችን ለማንሳት ያለመው ሊቨርፑል ሕልሙ መክኗል ።  አሰልጣኝ ኤሪክ ቴን ሐግ ቡድናቸው ማንቸስተር ዩናይትድ የዘመናት ባላንጣው ሊቨርፑልን ትናንት በኤፍ ኤ ካፕ ድል ማድረጉ ለእሳቸውም ሆነ ለቡድናቸው መነቃቃት እጅግ ወሳኝ እንደነበር ተናግረዋል ። ማንቸስተር ዩናይትድ መጀመሪያ ከ2 ለ1 ከዚያም ከ3 ለ2 መመራት ተነስቶ ፍጻሜውን ወደ 4 ለ3 ድል ገልብጦታል ።

 በኤፍ ኤ ካፕ የሩብ ፍጻሜ ፍልሚያ አሰልጣኝ ዬርገን ክሎፕ እቅዳቸው መክኖ ሽንፈት ተከናንበዋል
በኤፍ ኤ ካፕ የሩብ ፍጻሜ ፍልሚያ ከመጀመሪያው እና መጨረሻው ዐሥር ደቂቃዎች በስተቀር ሙሉ ለሙሉ የጨዋታ የበላይ የነበረው ሊቨርፑል የማታ ማታ በማንቸስተር ዩናይትድ ጉድ ሆኗል ። አሰልጣኝ ዬርገን ክሎፕ እቅዳቸው መክኖ ሽንፈት ተከናንበዋል ። ፎቶ፦ ከክምችት ማኅደርምስል Peter Byrne/dpa/picture alliance

በእርግጥ ከመጀመሪያው እና መጨረሻው ዐሥር ደቂቃዎች በስተቀር ሊቨርፑል ሙሉ ለሙሉ የጨዋታ የበላይ ነበር ማለት ይቻላል ። ምንም እንኳን ዳርዊን ኑኔዝ ግብዙ ጥረት ቢያደርግ የጨዋታውን መልክ ሊቀይሩ የሚችሉ ኳሶችን አምክኗል ። ሌላኛው ድንቅ ግብ ያስቆጠረው ሐርቬይ ኤሊዮት የፈጠረው ስህተት ማንቸስተር ዩናይትድ በመልሶ ማጥቃት ሊቨርፑልን ጉድ ያደረገ ብሎም የገደለ አጋጣሚ ነበር ። በጉዳት የትሬንት አርኖልድ አለመሰለፍ ሊቨርፑልን ከኋላ መስመር እጅግ ጎድቶታል ። አሰልጣኝ ዬርገን ክሎፕ  በክንፍ መስመር የጨዋታውን ፍጥነት ሲዘውር የነበረው አንድሪው ሮቤርትሰንን መቀየራቸውም ግራ የሚያጋባ ነበር ። 

በሌላ መልኩ የማንቸስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ኤሪክ ቴን ሀግ እየተመሩ በነበረበት የመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች ላይ ተከላካይ አስወጥተው ተጨማሪ አጥቂ በማስገባት ደፋር ውሳኔ ዐሳይተዋል ። ድፍረታቸው በእርግጥም ሠርቷል ። ብዙ ሲተች የነበረው አንቶኒ ተቀይሮ በመግባት ማንቸስተርን አቻ የምታደርገውን ወሳኝ ኳስ ከመረብ አሳርፏል ።  የ21 ዓመቱ አይቮሪኮስታዊ አጥቂ አማድ ዲያሎ በመልሶ ማጥቃት ድንቅ ግብ አስቆጥሮ መላ ኦልድትራፎርድን አስቦርቋል ። የማሸነፊያ ግቧን ካስቆጠረ በኋላ ግን መለያ ካናቴራውን በማውለቁ ቀደም ሲል ቢጫ ካርድ ዐይቶ ስለነበር በቀይ ከሜዳ ወጥቷል ። መልበሻ ክፍል ውስጥ ሆኖ ግን ብቻውን ደስታውን ለማጣጣም አልተገደደም ። ጨዋታው ወዲያው በማንቸስተር ዩናይትድ የ4 ለ3 ድል ተጠናቋል ።

በትናንቱ የእንግሊዝ ኤፍ ኤ ካፕ የሩብ ፍጻሜ ፍልሚያ ማንቸስተር ዩናይትድ የማሸነፍ መንፈሱን አነቃቅቷል ።
በትናንቱ የእንግሊዝ ኤፍ ኤ ካፕ የሩብ ፍጻሜ ፍልሚያ ማንቸስተር ዩናይትድ የማሸነፍ መንፈሱን አነቃቅቷል ። ፎቶ፦ ከክምችት ማኅደርምስል Dave Thompson/AP Photo/picture alliance

ማንቸስተር ዩናትድ ከአንድ ወር በኋላ በግማሽ ፍጻሜው የሚገጥመው እታችኛው ዲቪዚዮን የሚገኘው ኮንቬንትሪን ነው ። ያም በመሆኑ ወደ ፍጻሜ የማለፉ ጉዳይ በብዙዎች ዘንድ ሳይታለም የተፈታ ነው ። ምናልባትም አሰልጣን ኤሪክ ቴን ሀግ በፍጻሜው ማንቸስተር ሲቲን ወይንስ ቸልሲን ይሆን የምገጥመው እያሉም ይሆናል የሚያሰሉት ።

ቸልሲ ትናንት መደበኛ 90 ደቂቃ የጨዋታ ክፍለ ጊዜው ተጠናቆ በጭማሪ የባከኑ ደቂቃዎች ተጋጣሚው ላይስተር ሲቲን ጉድ አድርጎ 4 ለ2 አሸንፏል ። የማሸነፊያ ግቦቹን በ92 እና 98ኛው ደቂቃ ላይ በድንቅ ሁኔታ ያስቆጠሩት ካርኔይ ቹክዌሜካ እና ኖኒ ማዱዌኬ ናቸው ። በትናንቱ ጨዋታ ቸልሲ የበላይነቱን ዐሳይቶ ነው ወደ ግማሽ ፍጻሜ ማለፉን ያረጋገጠው ። ማንቸስተር ሲቲ ቅዳሜ ዕለት በቤርናርዶ ሲልቫ የመጀመሪያው አጋማሽ ግቦች ኒውካስትልን 2 ለ0 አሸንፏል ። ኮንቬንትሪ ሲቲ ደግሞ ዎልቭስን  በገዛ ሜዳው 3 ለ2 ድል አድርጎ ነው ለግማሽ ፍጻሜው የበቃው ።

ሻምፒዮንስ ሊግ

እጅግ በርካታ ተመልካቾችን እና አድናቂዎችን ያፈራው የሴቶች የአውሮጳ ሻምፒዮንስ ሊግ የሩብ ፍጻሜ ፍልሚያ ነገ እና ከነገ በስትያ ይከናወናል ። በነገው ዕለት፦ የሆላንዱ አያክስ አምስተርዳም ቡድን የእንግሊዙ ቼልሲን ይገጥማል ። የፖርቹጋሉ ቤኔፊካ ከፈረንሳዩ ሊዮ ጋ ይፋለማል ። ከነገ በስትያ ደግሞ፦ የስዊድኑ ቢኬ ሔይከን የፈረንሳዩ ፓሪ ሳን ጃርሞን ያስተናግዳል ። የስፔኑ ባርሴሎና የኖርዌዩ ኤስ ኬ ብራንን በብራን ስታዲየም ውስጥ ይገጥማል ። በሚቀጥለው ሳምንት በሚኖሩ የመልስ ግጥሚያዎች የግማሽ ፍጻሜ አላፊ ቡድኖች ይለያሉ ።

የሴቶች እግር ኳስ
እጅግ በርካታ ተመልካቾችን እና አድናቂዎችን ያፈራው የሴቶች እግር ኳስምስል Memmler/Eibner-Pressefoto/picture alliance

የወንዶች የሻምፒዮንስ ሊግ የሩብ ፍጻሜ አላፊ ቡድኖች የጨዋታ ድልድል ደግሞ ባሳለፍነው ሳምንት ወጥቷል ። በድልድሉ መሰረት፦ የእንግሊዙ አርሰናል የጀርመኑ ባዬርን ሙይንሽንን ይገጥማል ። ሌላኛው የእንግሊዝ ቡድን ማንቸስተር ሲቲ የደረሰው የስፔኑ ብርቱ ቡድን ሪያል ማድሪድ ነው ። የፈረንሳዩ ፓሪ ሳን ጃርሞ ከስፔኑ ባርሴሎና ጋ ሲጋጠም፤ ሌላኛው የስፔን ቡድን አትሌቲኮ ማድሪድ የጀርመኑ ቦሩስያ ዶርትሙንድን ያስተናግዳል ። የሩብ ፍጻሜ የመጀመሪያ ዙር ግጥሚያዎች የሚከናወኑት ከሦስት ሳምንት በኋላ ነው ። የካቲት 26 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ቡንደስሊጋ

በጀርመን ቡንደስሊጋ የእግር ኳስ ግጥሚያ መሪው ባዬርን ሌቨርኩሰን ዘንድሮ ዋንጫ ለማንሳት ግስጋሴውን ቀጥሎበታል ። ባዬርን ሌቨርኩሰን ትናንት ወደ ፍራይቡርግ አቅንቶ በ3 ለ2 ድል ተመልሷል ። የፍራይቡርግ አሰልጣኝ ክርስቲያን ሽትይሽ ከ12 ዓመታት ቆይታ በኋላ በፍራይቡርግየ አሰልጣኝነታቸው እንደማይቀጥሉ ይፋ አድርገዋል ። የ58 ዓመቱ አሰልጣኝ በቡንደስሊጋ አንድ ቡድንን ረዝም ጊዜ በማሰልጠን ሁለተኛው ሰው ለመሆን በቅተዋል።  የቡንደስሊጋው የምንጊዜም የረዥም ዓመታት አሰልጣኝ በመሆን የሚስተካከላቸው ያልተገኘው የሐይደንሀይም አሰልጣኝ ፍራንክ ሽሚድት ናቸው ። የ50 ዓመቱ አሰልጣኝ ቡድናቸው የሐይደንሀይምን ከ16 ዓመታት በላይ አሰልጥነዋል ። የባዬርን ሌቨርኩሰን የትናንቱ ድሉን ጨምሮ እስካሁን 70 ነጥብ ሰብስቦ ቡንደስሊጋውን በአንደኛነት ይመራል ። በ60 ነጥብ የሚከተለው ባዬርን ሙይንሽንም ቅዳሜ ዕለት ዳርምሽታድትን 5 ለ2 ድል አድርጓል ።

የ50 ዓመቱ አሰልጣኝ ፍራንክ ሽሚድት ሐይደንሀይምን ከ16 ዓመታት በላይ አሰልጥነዋል
የቡንደስሊጋው የምንጊዜም የረዥም ዓመታት አሰልጣኝ በመሆን የሚስተካከላቸው ያልተገኘው የሐይደንሀይም አሰልጣኝ ፍራንክ ሽሚድት ናቸው ። የ50 ዓመቱ አሰልጣኝ ቡድናቸው የሐይደንሀይምን ከ16 ዓመታት በላይ አሰልጥነዋል ምስል Tom Weller/dpa/picture alliance

56 ነጥብ ሰብስቦ ሦስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ሽቱትጋርት ሆፈንሀይምን ከትናንት በስትያ 3 ለ0 አሸንፏል ። በ50 ነጥብ ተከታዩ ቦሩስያ ዶርትሙንድ ትናንት አይንትራኅት ፍራንክፉርትን አስተናግዶ 3 ለ1 ሸኝቷል ። የደረጃ ሰንጠረዡ ግርጌ ላይ የሚገኘው ኮሎኝን 5 ለ1 ያደባየው ላይፕትሲሽ 49 ነጥብ ሰብስቦ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ። አይንትራኅት ፍራንክፉርት በ40 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ። ማይንትስ በ25 ነጥብ ወራጅ ቀጣናው ግርጌ 16ኛ ላይ ይገኛል ። ኮሎኝ እና ዳርምሽታድ በ18 እና 13 ነጥብ የደረጃ ሰንጠረዡ ግርጌ ላይ ሰፍረዋል ። በሳምንቱ ማገባደጃ ላይ በተደረጉ ሌሎች ግጥሚያዎች፦ ማይንትስ ቦሁምን 2 ለ0፤ ዑኒዮን ቤርሊን ቬርደር ብሬመንን 2 ለ1 አሸንፈዋል ። ለቡንደስሊጋው አዲስ የሆነው ሐይደንሀይም የአውሮጳ ግጥሚያዎች ላይ ብዙ ልምድ ካካበተው ቦሩሲያ ሞይንሽንግላድባኅ ጋ ተጋጥሞ አንድ እኩል ተለያይቷል ። ቮልፍስቡርግ በሜዳው በአውግስቡርግ የ3 ለ1 ሽንፈት ገጥሞታል ።  

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ታምራት ዲንሳ