1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያ በአፍሪቃ ጨዋታዎች ተጨማሪ ወርቅ አገኘች

ረቡዕ፣ መጋቢት 11 2016

ጋና አክራ ውስጥ በሚከናወነው የአፍሪቃ ጨዋታዎች የኢትዮጵያ ቡድን እንደተጠበቀው ተጨማሪ የወርቅ ሜዳሊያ አገኘ ። ዛሬ ጠዋት በተከናወነው የ20 ኪሎ ሜትር የወንዶች የርምጃ ፉክክር በአትሌት ምስጋና ዋቁማ ኢትዮጵያ ወርቅ አግኝታለች ። በተመሳሳይ የሴቶች የርምጃ ፉክክር በኢትዮጵያዊቷ አትሌት ስንታየሁ ማስሬ የብር ሜዳልያ ተገኝቷል ።

https://p.dw.com/p/4dvi1
ለኢትዮጵያ በ800 ሜትር የወርቅ ሜዳሊያ ያስገኘችው አትሌት ሴቶች ጽጌ ዱጉማ
ጋና አክራ ውስጥ በሚካሄደው የአፍሪቃ ጨዋታዎች ለኢትዮጵያ በ800 ሜትር የሩጫ ፉክክር የወርቅ ሜዳሊያ ያስገኘችው አትሌት ሴቶች ጽጌ ዱጉማ ። ውድድሯን በአንደኛነት ያጠናቀቀችው በ1:57.73 በመሮጥ ነውምስል Äthiopischer Leichtathletikverband

ጋና አክራ ውስጥ በሚከናወነው የአፍሪቃ ጨዋታዎች የኢትዮጵያ ቡድን እንደተጠበቀው ተጨማሪ የወርቅ ሜዳሊያ አገኘ ። ዛሬ ጠዋት በተከናወነው የ20 ኪሎ ሜትር  የወንዶች የርምጃ ፉክክር በአትሌት ምስጋና ዋቁማ ኢትዮጵያ ወርቅ አግኝታለች ። በተመሳሳይ የሴቶች የርምጃ ፉክክር ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ስንታየሁ ማስሬ ብር ሜዳልያ  አስገኝታለች ።ዛሬ የተገኙትን ሜዳሊያዎች ጨምሮ ኢትዮጵያ በሜዳሊያ ሰንጠረዥ ደረጃዋ ወደ 10ኛ ከፍ ብሏል ።  እስከ ሰኞ ከሰአት ድረስ የኢትዮጵያ ቡድን በሜዳሊያ ሰንጠረዥ 26ኛ ነበር ።  

ከኢትዮጵያ ቡድን ከበላይ ሞሮኮ በአምስት ወርቅ፤ ኤርትራ በስድስት ወርቅ 9ኛ እና 8ኛ ላይ ይገኛሉ ።  የኢትዮጵያ ቡድን እስካሁን አምስት የወርቅ፤ 3 የብር እና 1 የነሐስ ሜዳሊያ አግኝቷል ። የወርቅ ሜዳሊያ በተጨማሪ ያስገኙት፦ ንብረት መላክ በ10,000 ሜትር ወንዶች፤ በ3000 ሜትር መሰናከል ወንዶች ፉክክር ፍሬው ደቢሳ ናቸው ። በሴቶች የ5000 ሜትር ፉክክር መዲና ኢሳ እና በሴቶች 800 ሜትር ጽጌ ዱጉማ ተጨማሪ ወርቅ  አስገኝተዋል ። 

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ለውድድር ተዘጋጅተው
ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በጋና አክራ ለውድድር ተዘጋጅተውምስል Äthiopischer Leichtathletikverband

የኢትዮጵያ ቡድን ዛሬ ከሰአት በሚኖረው የሴቶች የጦር ውርወራ የፍጻሜ ፉክክር አትሌት የሺወርቅ አንማው እና ድንገቴ አዶላን ለተጨማሪ ሜዳሊያ ያወዳድራል ። ከሰአት በሚኖረው የ3000 ሜትር የሴቶች መሰናከል ሩጫ ውድድርም አትሌት ዓለማየሁ ወለተጂ፤ አትሌት ሎሚ ሙለታ እና አትሌት ፍሬሕይወት ገሠሠ ለሜዳሊያ ይጠበቃሉ ።  ኢትዮጵያውያኑ አትሌቶች ኬቻማን ዖጁሉ እና በቀለ ጂሎ የሚፎካከሩበት የሦስት ጊዜ መስፈንጠር ዝላይ የፍጻሜ ፉክክርም ዛሬ ከሰአት ይካሄዳል ። በወንዶች 800 ሜትር የፍጻሜ ፉክክር አትሌት ዮሐንስ ተፈራ ዛሬ ከሰአት ለሜዳሊያ ይፎካከራል ። የሴቶች እና የወንዶች የአራት አትሌቶች የ100 ሜትር የዱላ ቅብብል ፉክክርም ዛሬ ይከናወናል ።  በ400 ሜትር የተሳተፈው የወንዶች ቡድን ከግማሽ ፍጻሜው ውድድር ማለፍ ሳይችል ቀርቷል ።  የመጋቢት 9 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የጋና ዋና ከተማ አክራ በከፊል
ዘንድሮ የአፍሪቃ ጨዋታዎች የሚካሄድባት የጋና ዋና ከተማ አክራ በከፊልምስል Imago/UIG/T. Beddow

ሁለተኛ ሳምንቱን ባስቆጠረው እና የተለያዩ የስፖርት ዘርፎችን በሚያካትተው የአፍሪቃ ጨዋታዎች ግብጽ አሁንም በበላይነት ትመራለች ። ግብጽ እስካሁን 92 የወርቅ፤ 40 የብር እና 33 የነሐስ በድምሩ 165 ሜዳሊያዎችን ሰብስባለች ። ናይጄሪያ 31 የወርቅ፤ 22 የብር እንዲሁም 32 የነሐስ በድምሩ 85 ሜዳሊያዎችን ሰብስባ የሁለተኛ ደረጃ ይዛለች ። ደቡብ አፍሪቃ በ27 የወርቅ፤ በ29 የብር እና በ38 የነሐስ በድምሩ 94 ሜዳሊያ የሦስተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች ። 

የኤርትራ ቡድን 6 የወርቅ፤ 2 የብር እና 5 የነሐስ በድምሩ 13ሜዳሊያዎችን ሰብስቦ ከአንድ እስከ ዐሥር ካሉት ሃገራት ተርታ በመሰለፍ 8ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ። የፊታችን ቅዳሜ በሚጠናቀቀው የአፍሪቃ ጨዋታዎች፦ እግር ኳስ፤ የእጅ ኳስ፤ ነጻ ትግል፤ ባድሜንተን፤ የውኃ ዋና፤ ጁዶ፤ ቴኳንዶ፤ ብስክሌት፤ ቴኒስን ጨምሮ በ23 የስፖርት ዘርፎች ግጥሚያዎች ይኖራሉ ።   

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ታምራት ዲንሳ