1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የፋተርሽቴትን እና የዓለም ከተማ 20ኛ ዓመት ትስስር

ዓርብ፣ ሐምሌ 18 2006

ከአዲስ አበባ 185 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኘዉ የመረሃ ቤቴ አዉራጃ ዓለም ከተማ፤ በደቡባዊ ጀርመን በባቫርያ ግዛት የምትገኘዉ ፋተርሽቴትን ከተማ የእህትማማችነት ማህበርን መስርተዉ የትምህርት የባህል ልዉዉጥን ማድረግ ከጀመሩ ሃያ ዓመትን አስቆጠሩ።

https://p.dw.com/p/1Cidz
20 Jahre Partnerstadt zwischen Alem Katema und Vaterstetten
ምስል DW/A.Tadesse Hahn

ለዚሁ ቁርኝት መታሰብያ ማኅበሩ ጀርመን ቫባርያ ግዛት ወደምትገኘዉ ፋተር ሽቴትን የከተማዋን መስተዳድር ከንቲባና ሶስት ነዋሪዎች ጋብዞ 20ኛ ዓመቱን በደማቅ አክብሮአል። አዜብ ታደሰ ዝርዝር ዘገባ አላት
የዛሬ አስር ዓመት የዓለም ከተማና ፍተርሽቴትን እህትማማች ከተሞች ማኅበር የመሰረቱበትን አስረኛ ዓመት ያከበሩት ጀርመናዉያኑ ማኅበርተኞች ወደ ኢትዮጵያ በመጓዝ፤ ከአዲስ አበባ ዓለም ከተማ ድረስ በብስክሌት በመጓዝ ከነዋሪዉ ጋር በደማቅ ነበር ያከበሩት። ባለፈዉ ሳምንት 20ኛዉ ዓመት ሲከበር ደግሞ ከዓለም ከተማ አራት ነዋሪዎች በባቫርያዋ ግዛት ፋተር ሽቴትን ላይ ተጋብዘዉ በደማቅ አክብረዋል፤የማኅበሩ የኮሚቴ አባል መምህር ደሳለኝ ወንድምነህ ፤ ለከተማቸዉ ለዓለም ከተማ እድገት የሚበጁ ነገሮችን በቫቫርያ ግዛት እየተዘዋወሩ እንደተመለከቱና፤ እንደቀሰሙ ተናግረዋል።
በ10 የማኅበር አባላት የጀመረዉ፤ ይህ ማኅበር በፋተር ሽቴትን ከተማ በኩል 630 አባላትን እንዳቀፈ ተናግረዋል፤ የዓለም ከተማ ፋተርሽቴትን ማህበር ዋና ተጠሪ ጀርመናዊዉ አንቶን ሽቱፈን ተናግረዋል።
የዓለም ከተማ እና የጀርመኗ ከተማ የፋተርሽቴትን ማህበር ዋና ተጠሪ አንቶን ሽቴፈን ከዶቼ ቬለ ጋር ባደረጉት ንግግር፤ ማህበራችን 20ኛዉን ዓመት ሲያከብር ይላሉ፤ «የምስረታችን 20ኛ ዓመት በሁለት መንገድ ነዉ ያከበርነዉ፤ ከቀትር በፊት በፋተር ሽቴትን ከተማ በሚገኝ አንድ ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በተደረገ የስፖርት በዓል ሥነ-ስርዓት ነበር ። በዚህ ዝግጅት ላይ ጀርመን ፍራንክፈርት ከሚገኘዉ የኤትዮጵያ ቆንስላ ሁለት፤ ከፍተኛ እንግዶች ተካፍለዋል። ሁለተኛዉ ክፍል የአከባበር ሥነ-ስርዓት ደግሞ፤ ምሽት ላይ የተደረገ ሥነ-ስርዓት ነበር። በዚህ ዝግጅት ላይ ወደ 200 የሚሆኑ ተካፋዮች እንዲሁም ከፈረንሳይ የተጋበዙ አስራ አምስት እንግዶች እንዲሁም ከክሮየሽያ የተጋበዙ 15 እንግዶች ተገኝተዉ በደማቅ አክብረናል።»
ማህበራችን በዓለም ከተማና ፋተርሽታትን ከተሞች መካከል ያለዉን ነዋሪ ህዝብ በወንድማማችነት ማስተሳሰር ነዉ ያሉት የማኅበሩ ተጠሪ አንቶን ሽቴፈን፤ 20ኛዉ ዓመት አከባበር ለሁለቱም ከተሞች አስፈላጉ ነዉ።
«እንደኔ ይህ የአከባበር ሥነ-ስርዓት ለሁለቱም እህትማማች ከተሞች አስፈላጊ ነዉ፤ ብዬ እገምታለሁ። እዚህ ለሚገኘዉ የሁለቱ ከተሞች ትብብር ማኅበርም አስፈላጊ ነዉ። እንደሚታወቀዉ ከዓለም ከተማ መዉጫ መንገዶች ላይ የዓለም ከተማ አርማ ተሰቅሎ ይገኛል። የከተማችን ከንቲባ በጎርጎረሳዉያኑ አቆጣጠር 2003 ዓ,ም ከተማዋን ጎብኝተዉ ነበር። አሁንም ለመሄድ እቅድ ይዘዋል። እናም ቀስ በቀስ ማኅበራችን ወደ 630 ሰዎችን አቅፎ ይገኛል»
የዓለም ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ አጥላባቸዉ ፈለቀ ከተጋባዥ እንግዶቹ መካከል አንዱ ናቸዉ።
የዓለም ከተማ እና ፋተርሽቴትን የእህትማማች ከተሞች 20ኛ ዓመት ትስስርን ለማክበር ለ15 ቀናት በፋተር ሽቴትን ከተማ ቆይታ ያደረጉት ዓለም ከተማ ባለስልጣናትና ነዋሪዎች የፊታችን ቅዳሜ ሐምሌ 19/2006 ዓ,ም ወደ ሃገራቸዉ ይመለሳሉ።

አዜብ ታደሰ
ሂሩት መለሰ

20 Jahre Partnerstadt zwischen Alem Katema und Vaterstetten
ምስል DW/A.Tadesse Hahn
20 Jahre Partnerstadt zwischen Alem Katema und Vaterstetten
ምስል DW/A.Tadesse Hahn