1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት 20ኛ ዓመት፤ ገቢራዊነቱና ዉዝግቡ

እሑድ፣ ታኅሣሥ 12 2007

የዚያኑ ያክል ሕገ-መንግሥቱ የፀደቀበት ሃኛ ዓመት ከመከበሩ ከአንድ ቀን በፊት አዲስ አበባ ዉስጥ ለተቃዉሞ ሠልፍ አደባባይ ለመዉጣት የሞከሩ የከተማይቱ ነዋሪዎች፤ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎችና አባላት በፀጥታ አስከባሪዎች መደብደብ፤መዋከብ፤ በጅምላ እየታፈሱ መታሰራቸዉ ተዘግቧል።

https://p.dw.com/p/1E7oa
ምስል Fotolia/Maksym Yemelyanov

ኢትዮጵያ ፍትሐ-ነገሥት ከሚባለዉ ጥንታዊ የነገሥታት ደንብ ተላቃ ከዘመናዊ ሕገ-መንግሥት ጋር ከተዋወቀች -ዘንድሮ 84 ዓመት ደፈነች።በ1923 የመጀመሪያዉ ዘመናዊ ሕገ-መንግሥት መፅደቁ ከተነገረበት ጊዜ ወዲሕ በአማካይ በየሃያ ዓመቱ አዳዲስ ሕገ-መንግሥት ፀድቆላታል።በዚሕም ሰበብ ኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት ከማሻሻል ይልቅ ባጭር ጊዜ ብዙ በመቀያየር ከሚታወቁ ጥቂት ሐገራት አንዷ ናት።

አራተኛዉ የኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት ከፀደቀ-ሃያኛ ዓመቱን በቅርቡ ደፍኗል።ሥራ ላይ ከዋለ ደግሞ 19ኝ ዓመት ከመንፈቅ ግድም ቢሆዉ ነዉ።ሕገ-መንግሥቱ የዜጎችን ሰብአዊና ዴሞክራሲዊ መብቶችን፤ እኩልነትን፤ የተቋማትንና የማሕበራት ነፃነትን፤ የምርጫ ሥርዓትን፤ የገበያ ምጣኔ ሐብትን የብሔር መብትን በመደንገጉ እና ዓለም አቀፍ ሕግና ደንቦችንም የተቀበለ በመሆኑ ይደነቃል።

ገቢራዊነቱ ግን ብዙ አወዛጋቢ ነዉ።የኢትዮጵያ መንግሥት እንደሚለዉ ከልምድና ከአፈፃፀም ችግሮች በስተቀር በሕገ-መንግሥቱ የተደነገጉት መብቶች ሙሉ በሙሉ (በመንግሥት ባለሥልጣናት ቋንቋ ሳይሸራረፉ) ተጠብቀዋል፤ ወይም እየተጠበቁ ነዉ።ሃያኛዉ ዓመት ሰሞኑን አሶሳ ዉስጥ ሲከበርም ከዋዜማዉ ጀምሮ እስካሁንም ሕገ-መንግሥቱ ለሕዝቡ ያጎናፀፋቸዉን መብቶችና ነፃነቶች በመንግሥት መገናኛ ዘዴዎች በሰፊዉ ሲብራሩና ሲተነተኑ ሰምተናል።

የዚያኑ ያክል ሕገ-መንግሥቱ የፀደቀበት ሃኛ ዓመት ከመከበሩ ከአንድ ቀን በፊት አዲስ አበባ ዉስጥ ለተቃዉሞ ሠልፍ አደባባይ ለመዉጣት የሞከሩ የከተማይቱ ነዋሪዎች፤ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎችና አባላት በፀጥታ አስከባሪዎች መደብደብ፤መዋከብ፤ በጅምላ እየታፈሱ መታሰራቸዉ ተዘግቧል።ዓለም አቀፉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት CPJ ባገባደድነዉ ሳምንት ባወጣዉ አመታዊ ዘገባዉ የኢትዮጵያ መንግሥት ጋዜጠኞችን በማሰር፤በማዋከብ፤ በማሳደድ እና የፕሬስ ነጻነትን በመደፍለቅ ሐገሪቱን ከአፍሪቃ ሁለተኛ፤ ከዓለም አራተኛ ሐገር አድርጓታል።

Karte Äthiopien englisch

አምንስቲ ኢንተርናሽናል፤ ሑዩማን ራይትስ ዋች፤ ድንበር የላሽ ዘጋቢዎችን የመሳሰሉ ዓለም አቀፍ የመብት ተሟጋቾች፤ የአሜሪካ ዉጪ ጉዳይ ሚንስቴርን የመሳሰሉ የመንግሥታት ተቋማት- ከዉጪ፤ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች፤ ጋዜጠኞች፤ አቀንቃኞች ከዉስጥም ከዉጪም የኢትዮጵያ መንግሥት የራሱን ሕገ-መንግሥት እየደፈለቀ ዜጎቹን ያሰቃያል፤ ያስራል፤ ያዋክባል፤ ይገድላል፤ያሰድዳልም በማለት በተደጋጋሚ ይወቅሱታል። መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን (መያዶችን)ም ይዘጋል ይላሉ።

መንግሥት ተቺዎቹን፤ተቃዋሚዎቹንና ይቃወሙኛል ብሎ የሚጠረጥራቸዉን ወገኖች የሚያስር፤የሚወነጅልበት እንደ የፀረ-ሽብር፤የመያዶች እና የመሳሰሉ ደንቦቹም ሕገ-መንግሥቱን የሚፃረሩ ናቸዉ የሚሉ የሕግ-ባለሙዎችና የመብት ተሟጋቾች አሉ።የዉዝግቡን ሰበብ ምክንያት ነዉ የዉይይታችን ትኩረት።ሰዎስት እንግዶች አሉን።

ነጋሽ መሐመድ

ልደት አበበ