1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የቐጠር አሚር የጀርመን ጉብኝት

ረቡዕ፣ መስከረም 7 2007

የጀርመን ርእሰ ብሔር ዮአኪም ጋውክ ፣ ከቐጠር አሚር ሼክ ታሚም ቢን ሃማድ ኧል ታኒ ጋር ፣ ባደረጉት የ 20 ደቂቃ ውይይት ራሱን እስላማዊ መንግሥት እያለ ለሚጠራው አሸባሪ ሚሊሺያ ጦር፣ ያቺው ሀገር እርዳታ ትሰጣለች ስለመባሉ ቢያነሱም ፤አ ሚሩ ማስተባበላቸው ተነገረ።

https://p.dw.com/p/1DEoI
Merkel und Al-Thani PK 17.09.2014 Berlin
ምስል Getty Images/Adam Berry

አሚሩ ለአሸባሪ ቡድን አገራቸው ርዳታ እንደማትሰጥ ነው የተናገሩት። ከመራኂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክልና ርእሰ-ብሔር ጋውክ ጋር አሚሩ ከተወያዩ በኋላ ፤ በ IS ላይ በሚወሰደው ዓለም አቀፍ ርምጃ ቐጠርም ተባባሪ መሆኗን አስገንዝበዋል።

ጀርመን ፤ ለቐጠር የተለያዩ ጦር መሳሪያዎችን «ሊዮፓርድ የተሰኘውን ታንክ ጭምር በሽያጭ የምታቀርብ ሀገር በመሆኗ ፤ ጦር መሳሪያው ከማይፈለጉ ወገኖች እጅ እንዳይገባ የሚያሳስባት መሆኑንem ሳትገልጽ አልቀረችም። ለቐጠር ጦር መሣሪያ መሸጡን ፣ ክርስቲያን ዴሞክራቱ ፓርቲ ፤ አረንጓዴዎችና የግራ ፈለግ ተከታይ ፓርቲዎችም ይነቅፋሉ።

IS Kämpfer in Raqqa Syrien 16.09.2014
ምስል Reuters

ጋውክ ፣ በተጨማሪ፣ በዚያች ሀገር የሰብአዊ መብት ይዞታ በተለይ የውጭ ተወላጆች የሆኑ የስታዲየም ግንባታ ሠራተኞች ስለሚደርስባቸው በደል አንስተው እንደነበረ ቢታወቅም ፤ አሁን ሁኔታው መሻሻሉን ሼክ ታሚም ቢን ሃማድ ኧል ታኒ ተናግረዋል። ቐጠር፣ እ ጎ አ በ 2022 የዓለምን የእግር ኳስ ዋንጫ ውድድር እንድታዘጋጅ ያቀረበችውን ማመልከቻ ተቀብሎ የዓለም የእግር ኳስ ፌደሬሽን (FIFA) መወሰኑ የሚታወስ ነው።

ይህ በዚህ እንዳለ፣ በኢራቅና በሶሪያ፣ I S በተሰኘው እጅግ አክራሪ ታጣቂ ኅይል ውስጥ፣ የጀርመን ዜግነት ያላቸው አጥፍቶ ጠፊዎች ቁጥር ከፍ ብሎ መገኘት የጀርመንን ፌደራል መንግሥት እጅግ እንዳሳሰበው ተነገረ።

አንድ የጀርመን ተመራማሪ ቡድን ባደረገው ጥናት መሠረት ፤ እስካሁን አጥፍቶ በመጥፋት የተወሰዱ ቢያንስ 5 ርምጃዎች የተፈጸሙት ከጀርመን ፌደራል ሪፓብሊክ ወደ መካከለኛው ምሥራው በተጓዙ ሰዎች ነው። የሌሎች አጥፍቶ ጠፊዎች ሁኔታም በምርመራና ማጣራት ላይ መሆኑ ተመልክቷል። ከ «ዙዑድ ዶይቸ ትዛይቱንግ» NDR እና WDR የተውጣጣው መርማሪ ቡድን እንዳለው ፣ በ IS ትእዛዝ፤ የአጥፍቶ መጥፋት ርምጃዎቹ ከሞላ ጎደል ሁሉም፣ ኢራቅ ውስጥ በኩርዶች አውራጃዎችና በመዲናይቱ በባግዳድ ነው የተፈጸሙት። የምዕራቡ ዓለም የስለላ ድርጅቶች እንደሚሉት I S ሆን ብሎ ፣ ለፕሮፖጋንዳ እንዲያመቸው፤ ከአውሮፓ የሚሄዱትን ወንዶች ነው በአጥፍቶ መጥፋት ተግባር የሚያሠማራቸው።

ተክሌ የኋላ