1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሀማስ-እስራኤል ዘላቂ የተኩስ አቁም ስምምነት

ረቡዕ፣ ነሐሴ 21 2006

እስራኤል እና ሀማስ ትናንት የደረሱት የተኩስ አቁም ስምምነት ከትናንት አስራ ሁለት ሰዓት ጀምሮ እንደፀና ይገኛል። ተቀናቃኞቹ ወገኖች በግብፅ ሸምጋይነት ነበር ሰባት ሳምንታት ለሆነው የ2,002 ሰዎች ሕይወት ላጠፋው ውጊያ ገደብ ያልተደረገበት ስምምነት የደረሱት። በስምምነቱ መሠረት፣ በጋዛ ላይ የተጣለው ዕገዳም በከፊል እንደሚነሳ ተገልጾዋል።

https://p.dw.com/p/1D2hc
Palästinenser Israel Jubel in Gaza grüne Flaggen
ምስል picture-alliance/Ibrahim Khati

አዲሱ የተኩስ አቁሙ ደንብ ከተደረሰ ጀምሮ እስራኤል በጋዛ ያየር ጥቃት አለማካሄዷን ጋዛን የሚያስተዳድረው ሀማስም ወደ እስራኤል ሮኬት አለመተኮሱን የመገናኛ ብዙኃን ዘገባዎች አስታውቀዋል። በእስራኤል የሀማስ ቃል አቀባይ ሳሚ አቡ ዙህሪ ስምምነቱን በእስራኤል ላይ የተገኘ ድል ሲሉ አሞግሰውታል።
« በአጥፊው የእስራኤል ኃይል አንፃር ድል አድርገናል። በመጀመሪያ ደረጃ፣ በእግዚአብሔር ርዳታ፣ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ በሕዝባችን የመቋቋም ኃይል አማካኝነት ነው ያሸነፍነው። »
በሰው እና በንብረት ላይ ግዙፍ ጥፋት ለደረሰበት የጋዛ ሠርጥ የሰብዓዊ ርዳታ፣ መድሀኒት እና የግንባታ ቁሳቁስ መግባት ይችል ዘንድ ከእስራኤል እና ከግብፅ ወደ ጋዛ የሚወስዱት የድንበር መተላለፊያዎች እንዲከፈቱ እና የጋዛ አሳ አጥማጆች አሳ የሚያሰግሩበት አካባቢም እንዲስፋፋ ይፈቅዳል። በእስራኤል ጥቃት ልጆቻቸውን እና ብዙ ዘመዶቻቸውን ያጡት በሺዎች የሚቆጠሩ የጋዛ ነዋሪዎች የትናንቱ ስምምነት፣ አስቸኳይ ርዳታ እንደሚያስገኝላቸው ተስፋ አድርገዋል።
የአደራዳሪዋ ግብፅ ባለሥልጣናት እንዳመለከቱት፣ ቀጥተኛ ያልሆነው ድርድር በሁለቱ ቡድኖች መካከል ከአንድ ወር በኋላ ይቀጥላል።
የእስራኤል መንግሥት ቃል አቀባዕ ማርክ ሬጌቭ ስምምነቱ መደረሱን አዎንታዊ ሆኖ ቢያገኙትም፣ በትናንቱ ስምምነት የሰፈሩት ሀሳቦች ሁሉ ከአንድ ወር በፊት በቀረበውም ላይ የነበሩ ናቸው በሚል ሀማስ ስምምነቱን ለመቀበል አንድ ወር ያጠፋበትን ጊዜ ነቅፈዋል።

Grenzübergang Erez
የኤሬዝ መተላለፊያምስል DW/T. Krämer
Hamas-Sprecher Sami Abu Zuhri
ሳሚ አቡ ዙህሪምስል picture-alliance/Iandov

« ሀማስ ከአንድ ወር በፊት ውድቅ ያደረገውን ስምምነት ለምንድን ነው አሁን የተቀበለው በሚል ይጠይቃሉ። ይህ ሁሉ ደም መፋሰስ ሊወገድ በቻለ ነበር። »
በጋዛ በሺዎች የሚቆጠሩ ፍልሥጤማውያን በስምምነቱ መደረስ የተሰማቸውን ደስታ እና እፎይታ አደባባይ በመውጣት ገልጸዋል።
« በጣም ጥሩ ስሜታ ነው። ከዚህ የበለጠ ነገር አለ? አሳ ማጥመጃ ጀልባዎቻችንን 11,1 ኪሎሜትር ርቀት ድረስ መቅዘፍ እንደምንችል እና ይኸው የባህር ክልልም በድርድር ወደ 22, 2 ኪሎ ሜትር እንደሚስፋፋም ትናንት ሌሊት ተነገረን፣ ከዚህ የተሻለ ጥሩ ስሜት ሊኖር አይችልም። ዕገዳውን ማንሳት እና የድንበር መተላለፊያዎቹን መክፈት ጥሩ ነገር ነው። »
እስራኤል ጋዛን እአአ ሀምሌ ስምንት፣ 2014 ዓም ማጥቃት ከጀመረች ወዲህ ከፍተኛ የሀማስ ባለሥልጣናት እና የእሥላማዊው ጂሀድ ቡድን ተጠሪዎችም ለመጀመሪያ ጊዜ ባንድነት አደባባይ በመውጣት ለደጋፊዎቻቸው ንግግር ሲያሰሙ ታይተዋል።
በጋዛ ነዋሪዎች አንፃር ግን እስራኤላውያኑ ስምምነቱ የሚቀይረው ነገር እንደሌለ ነው የተናገሩት።
« መፍትሔ ያስገኛል ብየ አላስብም። የጦሩ ጥቃት በጠቅላላ ያስገኘው መፍትሔ የለም። ድሮ ወደነበርንበት ሁኔታ ነው የተመለስነው። »
የተኩስ አቁሙ ስምምነት መደረሱን ያሞገሱት የተመድ ዋና ጸሐፊ ፓን ኪ ሙን ስምምነቱ ለእስራኤል ፍልሥጤም ውዝግብ ዘላቂ የፖለቲካ መፍትሔ የሚገኝበትን መንገድ እንደሚከፍት ተስፋ ማድረጋቸውን ገልጸዋል።

Gaza hofft auf Wiederaufbau
ምስል DW/K. Shuttleworth

አርያም ተክሌ

ነጋሽ መሀመድ