1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኮንዶምን የማስተዋወቅ ስራ በኢትዮጵያ

ዓርብ፣ ጥቅምት 14 2007

ኢትዮጵያ ውስጥ ሰዎች ራስን ከኤድስ ፣ ካልታቀደ እርግዝና እና ከተለያዩ የአባለዘር በሽታዎች ለመከላከል፤ በኮንዶም መጠቀም እንዳለባቸው፤ ትምህርት የሚሰጡ የተለያዩ ማስታወቂያዎች በየጊዜው ቀርበዋል። ከዚህ በተጨማሪም ሰዎች በነፃ ወይም በገንዘብ መከላከያውን የሚያገኙበት አጋጣሚዎች ተፈጥረዋል።

https://p.dw.com/p/1Db5Y
Südafrika Weltaidstag Aidsschleife und Kondome
ምስል picture-alliance/dpa

ያለፉትን ዓመታት መለስ ብለን ስንቃኝ፤ ፈዋሽ መድሃኒት ባልተገኘለት እና እአአ ከታህሳስ 1981 ዓም ወዲህ ስርጭቱ መስፋፋቱ በታወቀው የኤድስ በሽታ ብዙ ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል። በሽታውን ለመከላከል እና የኤድስ ሰለባዎችን ቁጥር ለመቀነስም በኮንዶም መጠቀም ዋነኛው ዘዴ ሲሆን፣ በዚሁ አኳያ ኢትዮጵያ ውስጥ በርካታ ጠቃሚ ስልጠናዎች ተሰጥተዋል። ዲ ኬ ቲ ኢንተርናሽናል የተባለው ዓለም አቀፍ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ኢትዮጵያ ውስጥ« ህይወት ትረስት» በሚል መጠሪያ ኮንዶም ካስተዋወቀ 24 ዓመታት ተቆጠሩ። ከዚያን ጊዜ ወዲህም ኢትዮጵያ ውስጥ የኮንዶም ተጠቃሚውን ቁጥር ከሶስት ከመቶ ወደ 33 ከመቶ ከፍ ማድረግ መቻሉን ድርጅቱ ገልጾዋል። ኢትዮጵያ ውስጥ ቅርንጫፍ መስሪያ ቤት ከፍቶ በሚንቀሳቀሰው እና በተለይ በቤተሰብ ምጣኔ እና ፀረ ኤድስ አስተላላፊ ተሀዋሲ ፣ ማለትም፣ ኤች አይ ቪ መከላከያዎችን በማቅረብ በሚታወቀው ድርጅት ውስጥ የብሔራዊ ሽያጭ አስተባባሪ ክፍል ኃላፊ ፋሲል ጉተማ ድርጅቱ ኢትዮጵያ ውስጥ በኮንዶም የመጠቀም ባህልን ለማበረታታት ሰፊ ስራ እንዳከናወነ ገልፆልናል።

ሉላ ገዙ ዲ ኬ ቲ ኢንተርናሽናል ውስጥ ማስታወቂያ ከሰሩ ሶስት ወጣት ኢትዮጵያውያን አንዷ ናት። ላለፉት አራት ዓመታት በድርጅቱ ኮንዶምን በማስተዋወቁ ስራ ላይ ተሰማርታለች። ከድርጅቱ ጋር በነበራት ውል መሰረትም፣ በየቦታው ባሉት የኮንዶም ማስታወቂያዎች ላይ የሉላ ፎቶ የሚታይ ሲሆን፣ ማስታወቂያውን በተመለከተ ከሰዎች የተለያየ አስተያየት አግኝታለች። ምንም እንኳን ስራዋ አንዳንድ የህብረተሰቡን ክፍል ባያስደስትም፤ ወጣቷ እውቅ እንድታገን ዕድል ፈጥሮላታል። የገቢ ምንጭም ሆኖላታል። ስለሆነም በስራዋ ሌሎችን ብቻ ሳይሆን ራሷንም እንደጠቀመች ትናገራለች። ከሁለት ዩኒቨርስቲዎች በተለያዩ ዲግሪዎች የተመረቀችው ሉላ ያለፉት ዓመታት ስራዋን በሁለት መንገድ ነው የምትገልጸው።

Aids-Aufklärung in Südafrika
የኮንዶም አጠቃቀም ትምህርትምስል picture-alliance/dpa

ዲ ኬ ቲ ኢንተርናሽናል በአሁኑ ሰዓት ሉላን እና ባልደረባዋን የሚተኩ ወጣቶችን በመምረጥ ላይ ይገኛል። ድርጅቱ እጎአ ባለፈው ዓመት በዓለም ዙሪያ 548 ሚሊዮን ኮንዶም ሲሸጥ ከዚህም ውስጥ 58 ሚሊዮኑ ኢትዮጵያ እንደነበር በድረ ገፁ ላይ አስፍሯል። ዮኤስ ኤድ የተባለው ድርጅት ደግሞ በመጪው ዓመት 2015 ዓም 35 ሚሊየን ነፃ ኮምዶሞች ለኢትዮጵያ ለማቅረብ ዝግጁ መሆኑ ተጠቅሷል። « ኮንዶምን የማስተዋወቅ ስራ በኢትዮጵያ» በሚል ርዕስ ያጠናቀርነውን ዝግጅት በድምፅ ያገኙታል።

ልደት አበበ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ