1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኮሎኔል መንግሥቱ ና የሰሞኑ ተናፋሽ ወሬ

ሐሙስ፣ ሚያዝያ 17 2005

የዚምባብዌ መንግሥት ባለሥልጣናት ስለ መንግሥቱ ማረፍ ስለሚናፈሰው ወሬ የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ለሐራሬ የዶቼቬለ ወኪል አስታውቀዋል ።

https://p.dw.com/p/18NSn
ምስል AP

የቀድሞው የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያም አርፈዋል ሲል የዜምባብዌ ቴሌቪዥን መዘገቡን የሚጠቁሙ ፅሁፎች በአንዳንድ ብሎጎችና በፌስ ቡክ ተሰራጭተዋል ። ይሁንና የዚምባብዌ መንግሥት ባለሥልጣናት ስለ መንግሥቱ ማረፍ ስለሚናፈሰው ወሬ የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ለሐራሬ የዶቼቬለ ወኪል አስታውቀዋል ። ዴቼቬለ ዚምባብዌ ደውሎ በስልክ ያነጋገራቸው የ ኮሎኔል መንግሥቱ ዘመድ ነኝ ያሉ ግለሠብም የቀድሞው መሬ ሞተዋል የተባለው ሃሰት ነው ሲሉ ተናግረዋል ። ከ1983 ዓም አንስቶ ዚምባብዊ የሚኖሩት የቀድሞው የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያም ማረፋቸውን የሚጠቁሙ መረጃዎች በብሎጎችና በፌስ ቡክ ከወጣ ጥቂት ሳምንታት ተቆጥረዋል ። ማህበራዊ መገናኛ ብዙሃኑ የመረጃቸው ምንጭ የሚሉትም የዜምባብዊ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያን ነው ። ይሁንና የዚምባብዌ ማስታወቂያ ሚኒስቴር ስለተናፈሰው ወሬ የሚያውቀው ነገር እንደሌለ ነው ያስታወቀው ።

ሃራሪ ዚምባብዌ የሚገኘው የዶቼቬለ ወኪል ኮሉምቡስ ማቭሁንጋ የማስታወቂያ ሚኒስቴር ባለሥልጣናትን ስለጉዳዩ ጠይቆ ያገኘውን መልስ ነግሮናል ።

«ዛሬ ጠዋት ከማስታወቂያ ሚኒስቴር ሰዎችን ለማግኘት ሞክሬ ነበር ። አንድም ነገር አላረጋገጡም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ራሳቸው ስለሚናፈሰው ወሬ የሚያውቁት ነገር እንደሌለ የሆነ ነገር ካለም በይፋ እንደሚያሳውቁ ተናግረዋል ። »

Äthiopien Urteil Prozess gegen Mengistu und seine Minister
የደርግ ባለሥልጣናትምስል AP

ዶቼቬለ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያም መኖሪያ ቤት በመደውል ስለተናፈሰው ወሬ ምንነት ለማጣራት ባደረገው ሙከራ ያነጋገራቸው ግለሠብ ፣ መንግሥቱ ምንም የደረሰባቸው ነገር እንደሌና ጤነኛ መሆናቸውን ተናግረዋል ። ይህንኑ መረጃ በድምፅ ለመስጠት ፈቃደኛ ያልሆኑት ግለሠብ የሚወራው በሙሉም ውሸት ነው ብለዋል ። በደወልንበት ወቅት ኮሎኔል መንግሥቱ በቤት ውስጥ እንደሌሉና ሌላም ስለርሳቸው ሊነግረን የሚችል ሰው እንደሌለም ገልፀዋል ። ጋዜጠኛ ኮሎምቦስ እንደሚለው ግን ስለ መንግሥቱ የጤንነት ሁኔታ ትክክለኛውን መረጃ ማግኘቱ አዳጋች ነው ።

« ስለ መንግሥቱ ለመናገር አስቸጋሪ ነው ። በዚምባብዌ የሚገፉት ህይወት ሚስጥራዊ ነው ። ከፍተኛ ጥበቃ ከሚደረግላቸው ሰዎች አንዱ ናቸው ። ስለዚህ ጤናቸውም ሆነ የኑሮአቸው ሁኔታ በሚስጥር የሚጠበቅ ጉዳይ ነው ። ብዙዎች ስርሳቸውን ማግኘት አይችሉም ። በዚህ የተነሳም በሚናፈሰው ወሬ ውስጥ እውነት መኖሩን ለማወቅ አስቸጋሪ ያደርገዋል ። »

Portraitbild von Äthiopiens Ex-Diktator Mengistu Haile Mariam
ምስል picture alliance/dpa

ኮሎኔል መንግሥቱ ዚምባብዌ ውስጥ አሁን ምን እንደሚሰሩ በይፋ የሚታወቅ ነገር አለመኖሩን የጠቀሰው ጋዜጠኛ ኮሎምቦስ ሆኖም ከአመታት በፊት ለዚምባብዌው ፕሬዝዳንት ሮበርት ሙጋቤ ዛኑ ፒኤፍ ፓርቲ በአማካሪነት መስራታቸውን ተናግሯል ።

«በይፋ ምን እንደሚያደርጉ አይታወቅም ግን እንደሚገባን የዚምባብዌ መንግሥት አማካሪ በመሆን ሳይረዱ አልቀሩም ። እንዲያውም እጎአ በ 2005 የሮበርት ሙጋቤ ZANU PF ፓርቲ መንግግሥት በሐራሬና በሌሎች ከተሞች አንዳንድ ቤቶችን ለማፍረስ ሲሠማራ የዚህ ፕሮጀክት ጠንሳሽ ፣ ኮሎኔል መንግሥቱ ነበሩ ። ይህም የሆነው የተቃውሞ ወገን የድምፅ ድጋፍ እንዲቀነስበት ለማድረግ ነበር ። ከዚህ ሌላ ስለ እርሳቸው እምብዛም የምናውቀው ጉዳይ የለም ። የሚታወቅ ነገር ቢኖር በሐራሬ እንደሚኖሩና በምሥራቃዊው የአገሪቱ ደጋማ አውራጃ የእርሻ ቦታ ያላቸው መሆኑ ነው ። ይህም የዚምባብዌ መንግሥት ከመደባቸው ለም የእርሻ ቦታዎች አንዱ ነው ። »

ኮሎኔል መንግሥቱ በ17 አመታት የሥልጣን ዘመናቸው ፈፅመውታል በተባለው የዘር ማጥፋት ወንጀል በሌሉበት ሞት ተበይኖቦቸዋል ። የዚምባብዌ ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ሞርጋን ቻንጋራይ ከ 2 አመት በፊት በሰጡት ቃለ ምልልስ ሥልጣን ከያዙ ኮሎኔል መንግሥቱ ኢትዮጵያ እንዲመለሱ የሚያደርጉ መሆናቸውን ተናግረው ነበር ።

« ከ2 ዓመት በፊት የተቃዋሚው ወገን በአሁኑ ጠቅላይ ሚኒስትር የሚመራውን MDC ን አነጋግሬ ነበር ። ሥልጣን ላይ ከመጡ እርሳቸውን ይዘው ወደ ኢትዮጵያ እንዲመለሱ የሚያደርጉ መሆናቸውንም ነበር የMDC ሰዎች የገለጡልኝ ። ወደ አዲስ አበባ ሄደው ለፍርድ እንዲቀርቡ ሃራሬና የአዲስ አበባ ግንኙነትም እንዲሻሻል ነው የሚፈልጉት እርገጠኛ ነኝ የመንግሥት ለውጥ ከተደረገ ለኢትዮጵያ ተይዘው እንደሚሰጡ አያጠራጥርም ።»

ሂሩት መለሰ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ