የሱዳንና የደቡብ ሱዳን መንግሥታት፣ ከፍተኛ ልዑካን፣ አዲስ አበባ ውስጥ፤ በአፍሪቃ ኅብረት ሽምግልና በፖለቲካና ፀጥታ አጠባባቅ ረገድ በአንድ የመግባቢያ ሰነድ ላይ ተፈራርመዋል። ከአያንዳንዱ ሀገር 13 ከፍተኛ ልዑካን ተገኝተው በመግባቢያው ሰነድ ላይ እንዲፈርሙ ያበቁት ዋናው ሸምጋይ፤ የቀድሞው የደቡብ አፍሪቃ ፕቴዚዳንት ታቦ እምቤኪ ናቸው። «አንደኛው የጠብ ጫሪነት እርምጃ እንዳይኖር የሚያደርግ የመግባቢያ ሰነድ ነው። በዚህ ረገድ ሁለቱ አገሮች፤ ጠብ ሳይሆን፤ ትብብርን እንደሚመርጡ አረጋግጠዋል። ስብሰባው በተጨማሪ፣ ሌሎች ጉዳዮችንም አንስቶ መክሮአል። ሁሉንም አልዘረዝራቸውም። አንዳንዶቹ ጠቃሚ ጉዳዮች፤ ስብሰባው እንዳረጋገጠው፤ የጋራ ድንበር ተቆጣጣሪና አጣሪ ቡድን ተመድቦ ፣ ሥራውን ለሚያካሂድበት እርምጃ መንገድ መጠረጉ ነው። » ይህ በአንዲህ እንዳለ፤ የካርቱም መንግሥት መሪ ኦማር አል በሺር፤ ደቡብ ሱዳን ፣ ድፍድፍ ነዳጅ ዘይት ማምረቷን ማቆሟ ራስን በራስ እንደማጥፋት እርምጃ ይቆጠራል ማለታቸው ተጠቅሷል። ደቡብ ሱዳን ድፍድፍ ነዳጅ ዘይቷን በሰሜኑ በኩል በተዘረጋው ቧንቧ ለዓለም ገበያ ስታቀርብ ብትቆይም፤ ሰሜን ሱዳን 815 ሚሊዮን ዶላር የሚያውጣ ዘይት ሠርቃለች በማለት ድፍድፍ ነዳጅ የሚወጣባቸው ጉድጓዶች ለጊዜው እንዲዘጉ ማድረጓ ይታወሳል። ሌላ መሥመር በመሻት ከጎረቤት አገሮች ጋር መስማማቱንም የጁባ መንግሥት ማሳወቁ የሚታወስ ነው።
ሶማልያ ውስጥ የሚገኘው፤የአፍሪቃ ኅብረት ሰላም አስከባሪ ኃይል፣ከአል ቃኢዳ ጋር ግንኙነት እንዳለው የሚነገርለት ኃይል፣ አሸባብ፣ ከመዲናይቱ ከመቅዲሹ በስተምዕራብ ተጠናክሮ የሚገኝበትን ምሽግ ለማጥቃት ማቀዱን አንደኛው የጦር መሪ አስታወቁ። የአፍሪቃ ኅብረት ሰላም አስከባሪ ኃይል ምክትል ጦር አዛዥ ኦዴስ እንድውሙንሲ፣ ጦሩ፤ ከመቅዲሹ በስተምዕራብ 30 ኪሎሜትር ያህል ራቅ ብላ የምትገኘውን ከተማ አፍጎዬን ለመውረር በዝግጅት ላይ ነው ሲሉ አስታውቀዋል። አብዛኛው ደቡባዊው ሶማልያ፣ በመቅዲሹ የሚገኘውን ዓለም አቀፍ ድጋፍ የተሰጠውን አስተዳደር ለማፈናቀል በመዋጋት ላይ መሆኑ ይነገራል። የመቅዲሾውን መንግሥት የሚጠብቀው ፣ ከቡሩንዲ፣ ጂቡቲና ዩጋንዳ የተውጣጣ 9,700 ወታደሮች የሚገኙበት ጠንካራ ጦር ነው።ባለፈው ወር የአፍሪቃ ኅብረት አሁን 12 ሺ ድርሷል የሚባለው ጦር ወደ 17,731 ከፍ እንዲል የተባበሩት መንግሥታትን ማሳሰቡ ታውቋል። በሶማልያ፤ የአፍሪቃ ኅብረት ሰላም አስከባሪ ጦር፣ በተጨማሪ ኪሳማዩን ዒላማው ያደረገ መሆኑን የገለጹት ምክትል ጦር አዛዡ፤ ዝናብ ዘነመ -አልዘነመ፤ ፀሐይ ወጣች-አልወጣች፣ ኪሳማዩን በቁጥጥራችን ሥር እናውላለን »ብለዋል። ይህ በአንዲህ እንዳለ፤ አሸባብ በዛሬው ዕለት በአገሪቱ ዙሪያ፣ የኦሳማ ቢን ላደንን ተከታይ ለሆነው ኧል ቃኢዳየአሸባሪዎች መረብ ድጋፍ በመስጠት የፖለቲካ ስብሰባዎችን አካሂዷል ሲል AFP አስታውቋል። የአል ሸባብ ቃል አቀባይ፤ ሼክ አሊ መሀመድ ራጅ ፤«የአሸባብና የአል ቃኢዳ ውህደት የጠላትን ልብ ያፈርሳል» ማለታቸው ተጠቅሷል።
ግሪክ፤ አዲስ የቁጠብ አቅድ ተግባራዊ ታደርግ ዘንድ፣ የጀርመን የኤኮኖሚ ሚስትር ፊሊፕ ሮዖስለር ጫና ማሳደራቸው ተነገረ። ሮዖስለር በቴሌቭዥን እንደገለጡት ፤ አዲሱን እቅድ፣ ብዙኀኑ መደገፋቸው ማለፊያ ቢሆንም፤ ወሳኙ ፤ የመዋቅሩን ተኀድሶ ተግባራዊ ማድረጉ ነው ብለዋል። ግሪካውያን በሚወስዱት የቁጠባ እርምጃ ፣ እንደ ፖርቱጋላውያንና እስፓኛውያን ቁርጠኛነት አላሳዩም ያሉት ሮዖስለር ፣ አሁን፣ ሁሉም ነገር በራሳቸው እጅ መሆኑን ግሪካውኑ ሊገነዘቡት ይገባል ሲሉም አስገንዝበዋል። «አሁን ፤ ሁሉም ነገር ፣ በራሳቸው በግሪካውያን እጅ ነው ያለው። ግልጽ የሆኑ ቅድመ ግዴታዎች ብቻ አይደሉም የቀረቡት፤ በአውሮፓና በግሪክ መካከልም ስምምነት ተደርጎባቸዋል። እናም አሁን፣ በመጨረሻ በተግባር መተርጎም ይኖርባቸዋል። ሁሉም ነገር የሚጠበቀው በተግባር ላይ እመዋሉ ላይ ነው።» የግሪክ ጠ/ሚንስትር ሉካስ ፓፓዴሞስ፣ ድምጽ ከመሰጠቱ በፊት ባሰሙት ንግግር ላይ ፣ አዲሱ እቅድ ፣ ግሪክ ፣ ወደባሰ የድህነት አዘቅት እንዳትገባና ከዩውሮ ተጠቃሚ አገሮች አባልነት እንዳትወገድ ዓላማ ያደረገ ነው ብለዋል። እቅዱን በአገሪቱ በመላ አያሌ ህዝብ አደባባይ እየወጣ መቃወሙም ተነግሯል። በመዲናይቱ በአቴናና በተሰሎንቄ ከተሞች ብቻ፤ 100,000 ያህል ሰዎጽች ናቸው አደባባይ በመውጣት ተቃውሞአቸውን ያሰሙት። ከፖሊስ ጋር በተደረገው ግጭት፤ 120 ሰዎች መቁሰላቸውንና በዛ ያሉ ሱቆች በአሳት መለኮሳቸው አንዳንዶችም መመዝበራቸውን መገናኛ ብዙኀን አስታውቀዋል።
የአንድን ግለሰብ ድርጅትም ሆነ ሀገር የፈጠራ ውጤት የሚኮስሉ፣ ማለትም አስመስለው በመሥራት አላግባብ የንግዱ ትርፍ ተሳታፊዎችን ለመታገል የተደረገውን ዓለም አቀፍ ስምምነት ( "Anti-Counterfeiting Trade Agreement") በመቃወም አውሮፓ ውስጥ በተለያዩ ታላላቅ ከተሞች ባለፈው ቅዳሜ ሰልፍ ላካሄዱት ሰዎች ሥጋት፣ ግንዛቤው ያላቸው መሆኑን በጀርመን የህዝብ እንደራሴዎች ም/ቤት(Bundestag) የወግ አጥባቂዎቹ ፓርቲዎች፤ የህዝብ እንደራሴዎች ሥራ መሪ፣ ፔተር አልትማየር ገለጡ። የክርስቲያን ዴሞክራት ኅብረትና የክርስቲያን ሶሺያል ኅብረት የህዝብ እንደራሴዎች የፓርላማ ሥራ አስኪያጅ አልትማየር፤ ፤ የኢንተርኔት ጉዳይ ፤በጥሞና ውይይት የሚያሻው ነው ሲሉ በዛሬው ዕለት አስታወቀዋል። ጉዳዩ፣ በፖለቲካ አመራር ረገድ በጥሞና ይታያል። ይህ ማለት ግን ፤አመራሩ የራሱን ፖለቲካ መመርመሩን ያተዋል ማለት እንዳልሆነ አስረድተዋል። «ሁለት ነገሮችን ለይቶ ማየት ያሻል። አንደኛው የፈጠራ ውጤት ዝርፊያን መታገል አስፈላጊና ትክክለኛ እርምጃ ነው። ይህን ደግሞ በሀገር ውስጥና በኤኮኖሚ አጽናፋዊ ትሥሥር በተቆራኙት ሃገራት ዓለም አቀፍ እርምጃ ማስፈጸም ይቻላል። ይህን አብዛኞቹ ፤ ለሰልፍ አደባባይ የወጡት አይቃወሙትም። ሁለተኛው፤ ወጣቶችን የሚያሳስበው፤ የፈጠራ ውጤትን ዝርፊያ መታገል በሚል ስልት፤ የኢንተርኔት መሥመሮች የሚዘገቡት፤ አንዳንድ መረቦች ላይም ማዕቀብ የሚጣልበት ሁኔታ እንዳይፈጠር ነው። እንደሚመስለኝ፤ ሁለቱም ጉዳዮች በግልጽ ተለይተው መታወቅ አለባቸው። በኢንተርኔት መረብ መጠቀም፤ በአሁኑ ዘመን ፤ መሰረታዊ መብትና ፤ እጅግ ዐቢይ ግምት የሚሰጠው ጉዳይ ሲሆን፤ በፓርላማ የምንገኝ ሰዎች ደግሞ ፤ ስለምንፈልግውና በምንም ዓይነት ስለማንፈልገው ጉዳይ በጥሞና እንመክራለን።»
የብሪታንያ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ዊልያም ሄግ፣ ደቡብ አፍሪቃ ውስጥ የሚገኙ ሲሆን፤ በዚያም የሶሪያን ወቅታዊ ይዞታና በቅርቡ በለንደን እንዲካሄድ የታቀደውን ሶማልያን የሚመከተውን ጉባዔ በተመለከተ መመካከራቸው እንደማይቀር ተነግሯል። ለ 2 ቀናት በኬፕታውን የሚቆዩት ሄግ፤ ሰለሶሪያ ውዝግብና ስለሶማልያው ጉባዔ ሐሳብ የሚለዋወጡት ከደቡብ አፍሪቃ ሚንስትሮች ጋር ነው። ዊልያም ሄግ ፤ በምዕራባዊው ኬፕ ዩኒቨርስቲ በሚያሰሙት ዲስኩር፤ የደቡብ አፍሪቃና የብሪታንያ አዲስ ግንኙነት በሚል ርእስ ላይ እንደሚያተኩሩ ከለንደን የውጭ ጉዳይ ሚንስቴሩ ጽ/ቤት አስታውቋል።
ድሬስደን በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ፍጻሜ አቅራቢያ በአየር ክፉኛ የተደበደበችበትን 67 ዓመት አስባ ዋለች። 100 ገደማ የሚሆኑ ሰዎች በቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ዕለቱን ሲያስቡት፤ በከተማይቱ ጥንታዊ ከፊል፤ ከ 10,000 የሚበልጡ ሰዎች ሳይሰበሰቡ እንዳልቀሩ ተነግሯል። በሌላ በኩል ፤ ፓርቲዎች፣ አብያተ ክርስቲያንና ማኅበራት «ኒዎናዚስ» በመባል የታወቁት የቀድሞዎቹ ናዚዎች ተከታዮች፤ የተጠቀሰውን መታሰቢያ አስመልክተው ችቦ እያበሩ እንዳይወጡ ሁሉም እንዲቃወማቸው ጥሪ አስተላልፈዋል። ኒዎ ናዚዎቹ በያመቱ በዚሁ ዕለት በሚያስቡት በዓል፤ ጀርመናውያን በሁለተኛው የዓለም ጦርነት የጦር ወንጀል አልፈጸሙም እያሉ ሸምጥጠው ሲክዱ መቆየታቸው ተመልክቷል። በሁለተኛው የዓለም ጦርነት የጦር ተጓዳኝ መንግሥታቱ፣ ድሬስደንን እ ጎ አ የካቲት 13 እና 14, 1945 ዓ ም፤ክፉኛ በመደብደብ 25,000 ያህል ሰው መግደላቸው ታውቋል።
በዓመታዊው የዩናይትድ እስቱቴትስ የሙዚቃ ኢንዱስትሪዎች ሽልማት «ግራሚ አወርድስ» የ 23 ዓመቷ ወጣት እንግሊዛዊት ዘፋኝ ፣ አዴል፣ በ 6 የውድድር ነጥቦች ሁሉ በማሸነፍ «ወርቃማውን ግራማፎን» ተሸለመች። ይሁንና ደማቅ የደስታ በዓል እንደሚሆን ይጠበቅ የነበረው የሽልማት አሰጣጥ ሥነ ሥርዓት፣ የፖፕ ሙዚቃ ንግሥት የተባለችው እጅግ ከፍተኛ የሆነ የድምጽ እርከን ታድላ እ ጎ አ በ 1980ኛዎቹና 1990ኛዎቹ ዓመታት ከሴት ድምጻውያት ወደር ያልነበራት ዊትኒ ዩስተን ከትናንት በስቲያ ድንገት በ 48 ዓመቷ ከዚህ ዓለም በሞት በመለየቷ ኀዘይ ያጠላበት ነበረ። በዚሁ የሙዚቃ ሽልማት ለዊትኒ የተመልካቹን ስሜት የሚናካ መታሰቢያም ተድርጓል።