1. Inhalt
  2. Navigation
  3. Weitere Inhalte
  4. Metanavigation
  5. Suche
  6. Choose from 30 Languages

ዜና | 08.02.2012 | 17:22

አዲስ አበባ፤ በ 10 ሺ የሚቆጠሩ ሰዎች ከሰሜናዊው ኬንያ ተሰደዱ፤

የእርዳታ ሠራተኞች እንደሚገምቱት ፣ በሰሜናዊው ኬንያ 20 ሺ ያህል ሰዎች፣ በቅርቡ ባገረሸ ግጭት ሳቢያ  ወሰን ተሻግረው  የተሰደዱ መሆናቸውንና እርዳታ የሚያሻቸው መሆኑን አስታወቁ።የተባበሩት መንግሥታት፤ የሰብአዊ እርዳታ ጉዳይ መ/ቤት እንዳስታወቀው፤ በተቀናቃኝ ጎሳዎች ግጭት ሳቢያ ባለፉት ጥቂት ሳምንታት ፤ በ 10 ሺ የሚቆጠሩ ሰዎች ህይወ።ታቸውን ለማትረፍ ወደ ኢትዮጵያ ተሰደዋል። ለ 15,000 ያህል ሰወች፤ ምግብና ፕላስቲክ አንሶላ እንዲሁም ለ 3,000 ያህል ሰዎች የቤት ዕቃዎች መላኩም ተገልጿል። በሞያሌ አካባቢ፣ በግጦሽ ቦታ ሳቢያ ባለፈው ወር ፤ በጠብመንጃና በቆንጨራ በተደረገ  ውጊያ ቢያንስ 18 ሰዎች  መገደላቸው ታውቋል።

ካርቱም፤ በሱዳን የምግብ እጥረት እጅግ ማሥጋቱ ተነገረ፣

ግጭት በተከሠተባቸው የሱዳን 2 ክፍላተ -ሀገር ፣ ደቡብ ኮርዶፋንና «ብሉ ናይል» የምግብ እጥረት እጅግ ማሥጋቱን የገለጠው፣ የተባበሩት መንግሥታት  የምግብና ግብርና ድርጅት ባስቸኳይ ጥናት ይደረግ ዘንድ አሳሰበ። በሱዳን መንግሥት ወታደሮችና ፤ ቀድሞ ከደቡብ ሱዳን ነጻ አውጪዎች ጋር በአንድነት ተሰልፈው የተዋጉ የደቡብ ኮርዶፋን አማጽያን፤ በሚያደርጉት ውጊያ ሳቢያ የግብርናው እንቅሥቃሤ መገታቱ ተነግሯል። ባለፈው ዓመት በሰኔ ወር ፤ በደቡብ ኮርዶፋን ፤ በብሉ ናይል ክፍለ ሀገርም ካለፈው መስከረም ወር አንስቶ ውጊያ ከተጀመረ ወዲህ፤ 140,000 ያህል ሱዳናውያን ስደተኞች፣ ወደ ደቡብ ሱዳን ወይም ኢትዮጵያ ሳይሰደዱ እንዳልቀሩ የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ እርዳታ መ/ቤት አስታውቋል። በሱዳን ፤ የፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ  ልዩ መልእክተኛ ፤ Princeton Lyman የምግብ  እጥረቱ እጅግ አሳሳቢ በመሆኑ፤ ዋሽንግተን ፤ ያላካርቱም ፈቃድ እህል ማድረስ የሚቻልበትን እርምጃ እያሰበችበት መሆኑን ከማስጠንቀቂያ ጋር የዖማር አል በሺርን አገዛዝ አስጠንቅቃለች ብለዋል። 

እስታንሊ፣ የአርጀንቲናና የብሪታንያ ውዝግብ፣

በእንግሊዝኛ ፎክላንድ አይላንድስ  በእስፓኝ ቋንቋ Las Islas Malvinas በሚባሉት ደሴቶች ሳቢያ፣  እሰጥ አገባ በማገርሸቱ፣   አርጅንቲና፤ ፣ አካባቢው ፣ የጦርነት ቀጣና መሆን አይገባውም በማለት ፣ ለተባባሩት መንግሥታት የፀጥታ ጥበቃው ምክር ቤትና ለጠቅላላው ጉባዔ  አቤት! እንደምትል፤ ፕሬዚዳንቷ ወ/ሮ  Cristina Kirchner ቦይነስ አይረስ ውስጥ አስታወቁ። ብሪታንያ ዘመናዊ የጦር መርከብ ወደአካባቢው መላኳና ፤ የጦር ሄሊኮፕተር አብራሪው ፣ የንግሥት ኤልሳቤጥ የልጅ -ልጅ ፣ ልዑል ዊልያም   በዚያ እንዲገኝ መደረጉ፤ ደቡባዊውን  አትላንቲክ ወደ ጦር ቀጣናነት የሚለውጥ እርምጃ ነው ሲሉም ኪርኽነር ተናግረዋል። የአርጀንቲናዋ ፕሬዚዳንት ንግግር  ባሰሙበት ወቅት፣ ቤተ-መንግሥቱ  አቅራቢያ በመቶ የሚቆጠሩ አርጀንቲናውያን የተቃውሞ ሰልፈኞች በመሰብሰብ፤ «እንግሊዞች ከማልቪናስ ደሴቶች ውጡ!» የሚል መፈክር ማሰማታቸው ተጠቅሷል። አርጀንቲና ፤ እ ጎ አ ሚያዝያ 2 ቀን 1982 ዓ ም፤ ፎክላንድ ደሴቶችን ወራ እንደነበረና ከዚያም በባህርና የብስ በተካሄደ ብርቱ ውጊያ ፤ አርጀንቲና ተሸንፋ ለቃ ከወጣች 30 ዓመት ገደማ ሲሆን ፤ አሁንም የአርጀንቲና የደ።ሴቶቹ ይገቡኛል ጥያቄዋን እንደገና ያቀረበች ሲሆን ፤ ብሪታንያም አላስነካም ባይነትዋን አሳይታለች። m ክሪስቲና ኪርሽነር--- «እጅጉን ጥንቃቄ ለማድረግ ብንጥርም፤ ለድርጊቱ ሌላ ትርጓሜ ልናገኝለት አልቻልንም። የጠላት ኃይል የሚያወድም የጦር መርከብ  ላኩ፤ ልብ በሉ፤ ግዙፍና ዘመናዊ የጦር መርከብ ከአልጋወራሹ ጋር ነው የላኩት።»

ጀኔብ፤ ሶሪያና የተ መ ድ የሰብአዊ መብት ጥበቃ ኀላፊ፤

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብአዊ መብት ጥበቃ ዋና ኀላፊ ወ/ሮ ናቪ ፒሌይ፤በሶሪያ ለሲብሎች ጠበቃ ማድረግ ይቻል ዘንድ አጣዳፊ ዓለም-አቀፍ  እርምጃ ያሻል ሲሉ ጥሪአቸውን አሰሙ። የፀጥታ ጥበቃው ም/ቤት ጠንከር ባለ የጋራ እርምጃ ላይ አለመስማማቱ፤ ከሰብአዊ መብት ኮሚሽኑ የወጣው መግለጫ እንደሚለው ።  የሶሪያ ፈላጭ ቆራጭ  አገዛዝ፤ በሲቭሎች መኖሪያ ሠፈሮች ፣ ተቃውሞን አርቃላሁ በሚል ሰበብ፣ በጅምላ የግድያ እርምጃ እንዲወስድ ገፋፍቶታል ። ባለፈው ቅዳሜ፤ የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታ ጥበቃው ም/ቤት፣ በሶሪያ ላይ ጠንከር ያለ ውሳኔ ለማሳለፍ ያቀረበውን ረቂቅ ፤ ሩሲያና ቻይና ድምፅን በድምፅ የመሻር መብታቸው ውድቅ ያደረጉት መሆናቸው ይታወሳል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ፤ የሩሲያው ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ፣ ትናንት ደማስቆ ውስጥ ከሶሪያው ፕሬዚዳንት በሽር ኧል አሰድ ጋር ተገናኝተው ከተነጋገሩ በኋላ፤ አሰድ የኃይሉን እርምጃ ለማቆም ዝግጁ ናቸው ከማለታቸውም፤ ከተቃውሞው ወገን አንጻር አሰድ የሚፈጽሙትን ተግባር ከሞላ ጎደል ተገቢ አድረገው እንደሚመለከቱት ነው የጠቆሙት። «የሶሪያው ፕሬዚዳንት፤ በሀገሪቱ የኃይል እርምጃ ፤ ከየትኛውም ወገን ይወሰድ እንዲገታ ለማድረግ ኀላፊነታቸው መሆኑን ቃል ገብተውልኛል። ይህን ለማድረግ፤ ከሁለም የሶሪያ የፖለቲካ ኃይሎች ጋር  መወያያት የግድ ይላል። በዛሬው ዕለት ፤ ይህ ተግባር የሚቀጥል ስለመሆኑ ፤ ከሶሪያው ፕሬዚዳንት ማረጋገጫ አግኝተናል።» ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ የዐረብ መንግሥታት ማኅበር ፤ በሶሪያ ያሰማራቸው ታዛቢዎች አገር ለቀው  እንዲወጡ መመሪያ መሰጠቱን ፤ ከማኅበሩ ጽ/ቤት ከካይሮ የተገኘው ዜና ያስረዳል። የዐረብ መንግሥታት ማኅበር ታዛቢዎች፤ የሶሪያ ጦር ፤ ከከተሞች እንደሚወጣና  የተቃውሞ የፖለቲካ ሰዎች ሁሉ እንደሚለቀቁ  በእማኝነት ለመቆጣጠር ባለፈው ታኅሳስ ወር ነበረ የተላኩት። ካለፈው ሳምንት ማለቂያ ወዲህ፤ ሆምስ በተባለችው ከተማ፤ ከ 200 በላይ ሲብሎች መገደላቸው ታውቋል ።

መቅዲሹ፤ በአጥፍቶ ጠፊ ቢያንስ 9 ሰዎች ተገደሉ፣መቅዲሹ፤ በአጥፍቶ ጠፊ ቢያንስ 9 ሰዎች ተገደሉ፣

በሶማልያ መዲና በመቅዲሹ፤ አንድ አጥፍቶ ጠፊ ሳይሆን እንዳልቀረ የተጠረጠረ ሰው ከተሽከርካሪ ባነጎደው ፈንጂ ሳቢያ ቢያንስ 9 ሰዎች መሞታቸውንና 34 መቁሰላቸውን ፖሊስ አስታወቀ። ፍንዳታው የደረሰው የፓርላማ አባላት ከሚያዘወትሩበት ሆቴል አቅራቢያ ነው። 

ዋሽንግተን፤ የሶማልያው የባህር ላይ ውንብድናና ወጪው፤

ከሶማልያ ጠረፍ ፈንጠር ብሎ ሲካሄድ በቆየው የባህር ላይ ውንብድና ባለፈው 2011 ጎርጎሪዮሳዊው ዓመት ብቻ፤ ዓለምን 7 ቢሊዮን ዶላር ያክል ገንዘብ ማስወጣቱ ተነገረ። ይህም  ለጦር እርምጃ፤ ለመርከብ ጠባቂዎችና ለዚህም የሚያስፈልገውን መሣሪያ ጨምሮ ያስወጣውን ከ 2 ቢሊዮን ዶላር በላይ ያካትታል። በአማካዩ ለባህር ላይ ወንበዴዎች በተናጠል እርምጃ የተከፈለው ካሣ 5 ሚሊዮን ዶላር እንደነበረ፤ በጠቅላላ ግን በዚያው ዓመት ብቻ 160 ሚሊዮን ዶላር መድረሱን ፣ አንድ የባህር ላይ ውንብድና ተከታታይ ቡድን አስታውቋል። ከሶማልያ ጠረፍ እየተነሱ የንግድ መርከቦችን ሲጠልፉ የነበሩና ያሉ   የባህር ላይ ወንበዴዎች ፤ እ ጎ አ በ 2011 ዓ ም ብቻ 237 ጊዜ ነው ጥቃት የሠነዘሩት። ይህም በዓለም ዙሪያ ከሚያጋጥመው የባህር ላይ ውንብድና በሶማልያ ጠረፍ  አካባቢ የተከናወነው ከግማሽ በላይ መሆኑን ዋና ጽ/ቤቱ በለንደን የሚገኘው ዓለም አቀፍ የንግድ መርከቦች ማኅበር አስታውቋል።

በርሊን፣ የጀርመንና የካዛኽስታን ስምምነት፣

ጀርመንና በአንድ ፈላጭ- ቆራጭ መሪ  በምትመራው ካዛኽስታን  መካከል በርሊን ውስጥ የጥሬ ሀብት አቅርቦትን የሚመለከት ውል መፈራረማቸው ተነገረ። ውሉ የተፈረመው መራኂተ-መንግሥት አንጌላ ሜርክልና የካዛኽስታኑ ፕሬዚዳንት ኑርሱልታን ናሳርባየቭ በተገኙበት  ነው። ካዛኽስታን፤ ለረቂቅ የኢንዱስትሪ ውጤቶች እጅግ ተፈላጊ የሆነ የከበረ ድንጋይ ያላት ሀገር ናት። ብርቅ የሆኑ፤ 97 ከመቶ ፣ ለአንዳንድ ኢንዱስትሪዎች የሚበጁ ማዕድናት እስካሁን በአመዛኙ የሚገዙት ከቻይና ነው። ከውሉ መፈራረሙ ሌላ ፤ ሜርክል፤ ባለፈው ታኅሳስ፤ ሻናኦዘን በተባለችው ከተማ፤ በተቀሰቀሰው ሁከት አዘል ተቃውሞ ፤ ጸጥታ አስከባሪዎች ፤ ቢያንስ 17 የነዳጅ ዘይት ሠራተኞችን የገደሉበት ድርጊት በዝርዝር እንዲጣራ በጥብቅ አሳስበዋል። 

ቪስባደን፤ በ 2011 ፣ የጀርመን ወጪ ንግድ አንድ ሚሊያርድ ዩውሮ ደረሰ፣

ጀርመን በ 2011 ጎርጎሪዮሳዊው ዓመት ከሌሎች አገሮች ጋር ባደረገችው የንግድ ልውውጥ፤ አንድ ሚሊያርድ ዩውሮ ገቢ ማግኘቷን ፣ በቪስባደን ከተማ የሚገኘው የፈደራሉ መንግሥት የእስታቲስቲክስ ጽ/ቤት አስታወቀ። አገሪቱ፤ ከውጭ ያስገባችውም የተለያየ ምርት መጠን እንደ ወቺው ንግድ ክብረወሰን መያዙ ታውቋል። የኤኮኖሚ ሚንስትር ፊሊፕ ሮዖስለር፤ ይህ የሚያሳየው የጀርመን ኤኮኖሚ የተደላደለ መሆኑን ነው ብለዋል። TY/NM