1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጥቅምት 27 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ ጥቅምት 26 2016

ክብረወሰን በተሰበረበት የኒውዮርክ የማራቶን ሩጫ የወንዶች ፉክክር ኢትዮጵያ ለድል በቅታለች ። በሴቶች ተመሳሳይ ብርቱ ፉክክር የሁለተኛ ደረጃ የኢትዮጵያ ሆኗል ። በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ የአንድ ከተማዎቹ ቶትንሀም እና ቸልሲ ዛሬ ማታ ወሳኝ ግጥሚያ አላቸው ። ሊቨርፑል ከታችኛው ዲቪዚዮን ባደገ ቡድን ተሸንፎ ከመዋረድ ትናንት ለጥቂት ተርፏል ።

https://p.dw.com/p/4YT7A
ፖላንዳዊቷ የሜዳ ቴኒስ ምርጥ ተጨዋች ኢጋ ስዊያቴክ 
ፖላንዳዊቷ የሜዳ ቴኒስ ምርጥ ተጨዋች ኢጋ ስዊያቴክ የቤላሩስ ተፎካካሪዋ አሪና ሳባሌንካን ትናንት በግማሽ ፍጻሜ 6 ለ3 እና 6 ለ2 አሸንፋ ለፍጻሜ ቀርባለች ። ፎቶ፦ ከማኅደርምስል Tetsu Joko/The Yomiuri Shimbun/AP Photo/picture alliance

ክብረወሰን በተሰበረበት የኒውዮርክ የማራቶን ሩጫ የወንዶች ፉክክር ኢትዮጵያ ለድል በቅታለች ። በሴቶች ተመሳሳይ ብርቱ ፉክክር የሁለተኛ ደረጃ የኢትዮጵያ ሆኗል ። የኢትዮጵያእግር ኳስ ፌዴሬሽን ለብሔራዊ ቡድኑ አዲስ ዋና አሰልጣኝ ሾሟል ። በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ የአንድ ከተማዎቹ ቶትንሀም እና ቸልሲ ዛሬ ማታ ወሳኝ ግጥሚያ አላቸው ። ሊቨርፑል ከታችኛው ዲቪዚዮን ባደገ ቡድን ተሸንፎ ከመዋረድ ትናንት ለጥቂት ተርፏል ። በርመስን የግብ ጎተራ ያደረገው ማንቸስተር ሲቲ በአይበገሬነቱ ቀጥሏል ። አርሰናል ነጥብ በመጣል ግስጋሴውን ገትቷል ። በጀርመን ቡንደስሊጋ የብዙ ጊዜያት ተፎካካሪዎቹ ባዬርን ሙይንሽን እና ቦሩስያ ዶርትሙንድ ተጋጥመው ባዬርኖች በድል ተመልሰዋል ። ተጨማሪ ዘገባዎች ይኖሩናል ።

አትሌቲክስ

ኢትዮጵያዊው አትሌት ታምራት ቶላ በኒው ዮርክ ማራቶን ውድድር የቦታውን አዲስ ክብረ ወሰን በማስመዝገብ ለድል በቃ ። ትናንት በተከናወነው የማራቶን ሩጫ አትሌት ታምራት 1ኛ በመውጣት አሸናፊ የሆነው 2:04.58 በመሮጥ ነው ። በዚህም በኬኒያዊው ሯጭ ጂዮፍሬይ ሙታይ ለ12 ዓመታት ተይዞ የቆየውን የቦታውን ክብረወሰን (2:05:06) መስበር ችሏል ። ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት ሹራ ቂጣታ 2:07:11 በመሮጥ የ3ኛ ደረጃ ይዞ አጠናቋል ። የሁለተኛ ደረጃ ያገኘው ኬኒያዊ አትሌት አልበርት ኮሪር ከታምራት ቶላ በስምንት ሰከንድ ብቻ ተቀድሟል ። ጀርመናዊው ሔንድሪክ ፕፋይፈር 12ኛ ደረጃ ያገኘ ሲሆን፤ የገባበት ሰአት ለኦሎምፒክ የሚያበቃ ግን አይደለም ።

አትሌቲክስ፦ ሯጮች ሲሮጡ ። ፎቶ ከማኅደር
አትሌቲክስ፦ ሯጮች ሲሮጡ ። ፎቶ ከማኅደርምስል Charlie Neibergall/AP/picture alliance

የጥቅምት 19 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

በሴቶቹ ተመሳሳይ የኒው ዮርክ ማራቶን የሩጫ ፉክክር፦ ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ለተሰንበት ግደይ   2:27:29 በመሮጥ 2ኛ ደረጃ ይዛ አጠናቃለች ። የሁለት ጊዜያት የ5000 ሜትር የዓለም ባለድል ለመሆን የበቃችው ኬኒያዊቷ ሄለን ኦቢሪ የውድድሩ አሸናፊ መሆን ችላለች ። ሄለን ለድል የበቃችው አራት ሯጮች እስከ መጨረሻው ብርቱ ፉክክር ካደረጉበት ቡድን ውስጥ 2:27:23 ሮጣ በማጠናቀቅ ነው ።

እግር ኳስ

የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የቀድሞ ተጨዋች ገብረመድህን ኃይሌን የብሔራዊ ቡድኑ አዲስ ዋና አሰልጣኝ  አድርጎ ዐርብ ዕለት ሾሟል ።  የብሔራዊ ቡድኑን ለአንድ ዓመት እንዲያሰለጥኑ ውል የፈረሙት  አሰልጣኝ  ገብረመድህን ኃይሌ በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ መድህን እግር ኳስ ቡድንንም ደርበው ያሰለጥናሉ ።

ፌዴሬሽኑ ከዋልያዎቹ የቀድሞ ዋና አሰልጣኝ ውበቱ አባተ ጋ ባሳለፍነው ዓመት በስምምነት መለያየቱን ይፋ ካደረገ በኋላ የቴክኒክ ዳሬክተሩ ዳንኤል ገብረማርያምን በጊዜያዊ አሰልጣኝነት ሾሟቸው ነበር ። የቴክኒክ ዳሬክተሩ ሥራቸውን ካጠናቀቁ በኋላ ግን  ብሔራዊ ቡድኑ ያለ አሰልጣን ቆይቶ ነበር ። ፌዴሬሽኑ የውጭ ሀገር አሰልጣኝ የመቅጠር ፍላጎት እንደነበረውም ይታወቃል ። የስፖርት ጋዜጠኛ ዖምና ታደለ  ፌዴሬሽኑ በጠራው የዐርብ ዕለቱ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ታድሟል ። ዖምና አዲሱ አሰልጣኝ የተሰጣቸው ኃላፊነት እና ቀጣይ ግጥሚያዎች በቅርቡ የሚካሄዱ በመሆኑ ጊዜው አችር ነው ብሏል ። 

ፕሬሚየር ሊግ

የፕሬሚየር ሊግ በከፊል
የፕሬሚየር ሊግ በከፊል ። የሊቨርፑል ተጨዋቾች ። ፎቶ፦ ከማኅደርምስል Zac Goodwin/empics/picture alliance

የለንደን ከተማ ተፎካካሪዎቹ ቶትንሀም እና ቸልሲ ዛሬ ማታ ወሳኝ ግጥሚያ አላቸው ። አንደኛው በደረጃ ሰንጠረዡ አንደኛነት ለመስፈር ሌላኛው ከቁልቁለት ጉዞው ፋታ ለማግኘት ። ቶትንሀም ዛሬ በቀረው ተስተካካይ ጨዋታ ካሸነፈ የደረጃ ሰንጠረዡን በ27 ነጥብ ከሚመራው ማንቸስተር ሲቲ በሁለት ነጥብ በልጦ መሪነቱን መረከብ ይችላል ማለት ነው ። ዕድል በ12 ነጥቡ እና በ2 የግብ ክፍያው 13ኛ ደረጃ ላይ ለሚቃትተው ቸልሲ ከሆነች ደግሞ፦ የዛሬው ተስተካካይ ጨዋታ ድል ወደ ዐሥረኛ ደረጃ መሸጋገር ያስችለዋል ። ክሪስታል ፓላስ በ15 ነጥብ በ3 የግብ እዳ ዐሥረኛ ደረጃ

ላይ ይገኛል ።

የጥቅምት 12 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ትናንት የደጋፊዎቹን ትንፋሽ ያሳጠረው ሊቨርፑል የማታ ማታ በተገኘች ግብ ከሉቶን ታውን ጋር አንድ እኩል በመውጣት ወሳኝ ነጥብ ተጋርቶ ተመልሷል ። ሊቨርፑል እንደ አርሰናል 24 ነጥብ ሰብስቦ በተመሳሳይ የግብ ክፍያ ግን ደግሞ በአንድ የግብ እዳ የሦስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ።

በትናንቱ ግጥሚያ በደጋፊያቸው ፊት ጠንካራ ተፎካካሪ የነበሩት የሉቶን ታውን ተጨዋቾች አሸናፊ ልታደርጋቸው ትችል የነበረችውን ግብ ያስቆጠሩት 80ኛው ደቂቃ ላይ ነበር ። ከዚያ ቀደም ብሎ ሊቨርፑል ተደጋጋሚ የግብ ሙከራዎችን አድርጎ ነበር ። 80ኛው ደቂቃ ላይ ግን በግሩም የኳስ ቅብብል እና የቡድን ሥራ ታሂቲ ቾንግ ግብ ሲያስቆጥር ሊቨርፑል ወደ መርበትበት ነው የተሻገረው ። በተደጋጋሚ ጥረት ግን መደበናው የጨዋታ 90 ደቂቃ ተጠናቆ በባከነው 5ና ደቂቃ ላይ ሉዊስ ዲያዝ ሊቨርፑልን ከጉድ ታድጓል ።  

ሉዊስ ዲያዝ  «ነጻነት ለአባቴ» የሚል ጽሑፍ ካናቴራው ላይ ዐሳይቷል
አባቱ በሸማቂዎች የታገዱበት የሊቨርፑል አጥቂ ሉዊስ ዲያዝ ግቧን ካስቆጠረ በኋላ መለያውን ከፍ አድርጎ ካናቴራው ላይ ልብ የሚነካ ጽሑፍ አስነብቧል ። «ነጻነት ለአባቴ» የሚል ጽሑፍ ካናቴራው ላይ ዐሳይቷል ምስል Richard Bowcott/IPS/Shutterstock/IMAGO

ሉዊስ ዲያዝ ግቧን ካስቆጠረ በኋላ መለያውን ከፍ አድርጎ ካናቴራው ላይ ልብ የሚነካ ጽሑፍ አስነብቧል ። «ነጻነት ለአባቴ» ሉዊስ ዲያዝ በአጋቾች የታፈኑት አባቱ እንዲለቀቁ ካናቴራው ላይ  መልእክት ያስተላለፈበት ተማጽኖ ። የሉዊስ ዲያዝ አባትን ያገተው ብሔራዊ የነጻነት ጦር (ELN) የተሰኘው የኮሎምቢያው ሸማቂ ታጣቂ ቡድን ነው ። የቤተሰብ አስተዳዳሪ ታታሪ አባቴን እባካችሁ ልቀቁት ሲልም ለሸማቂዎቹ ሌላ የጽሑፍ መልእክት አስተላልፏል ።

ትናንት ኖቲንግሀም ፎረስት አስቶን ቪላን 2 ለ0 አሸንፏል ። አርሰናል ቅዳሜ ዕለት በኒውካስል የ1 ለ0 ሽንፈት ገጥሞታል ። ክሪስታል ፓላስ በርንሌይን 2 ለ0፤ ሼፊልድ ዩናይትድ ዎልቨርሀምፕተንን 2 ለ1 አሸንፈዋል ። ብሬንትፎርድ ዌስትሀምን 3 ለ2 ማንቸስተር ዩናይትድ ፉልሀምን 1 ለ0 ድል አድርገዋል ። ኤቨርተን ከብራይተን አንድ እኩል ሲለያይ፤ ማንቸስተር ሲቲ በርመስን 6 ለ1 የግብ ጎተራ አድርጎታል ። ለበርመስ ሉዊስ ሳኒስቴራ ብቸኛዋን ግብ 74ኛው ደቂቃ ላይ አስቆጥሯል ። የማንቸስተር ሲቲ ስድስት ግቦች በጄሬሚ፣ በርናርዶ ሲልቫ፣ ማኑዌል አካንጂ፣ ፊል ፎዴን እና ናታን አኬ ተቆጥረዋል ።

የጥቅምት 5 ቀን፣ 2016 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ቡንደስሊጋ

  የባዬር ሙይንሽን ቦሩስያ ዶርትሙንድን 4 ለ0 ኩም አድርጎታል
ወደ ቦሩስያ ዶርትሙንድ ያቀናው የባዬር ሙይንሽን ቡድን ተጋጣሚውን 4 ለ0 ኩም አድርጎታል ምስል Revierfoto/IMAGO

በጀርመን ቡንደስሊጋ  የዘመናት ተፎካካሪውን ለመግጠም ወደ ቦሩስያ ዶርትሙንድ ያቀናው የባዬር ሙይንሽን ቡድን ተጋጣሚውን 4 ለ0 ኩም አድርጎታል ። ለባዬርን ሙይንሽን አራቱን ግቦች ሁለት ሁለት ያስቆጠሩት ዳዮት ኡፓሜካኖ እና ሔሪ ኬን ናቸው ። በዚህም ባዬርን ሙይንሽን  26 ነጥብ ይዞ በቡንደስሊጋው የሁለተኛ ደረጃ ላይ መስፈር ችሏል ። መሪው ባዬር ሌቨርኩሰን ከትናንት በስትያ ዑኒዮን ቤርሊንን 3 ለ0 ድል አድርጓል ። ከባዬርን ሙይንሽን በሁለት ነጥብ ይበልጣል ። ሽቱትጋርት በ21 ነጥብ የ3ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ። በሀይደንሀይም ትናንት የ2 ለ0 ሽንፈት ገጥሞታል ። ቦሩስያ ዶርትሙንድ በተመሳሳይ ነጥብ ሆኖም በግብ ክፍያ ልዩነት 4ኛ ደረጃ ላይ ሰፍሯል ።  በማይንትስ የ2 ለ0 ሽንፈት የገጠመው ላይፕትሲሽ 20 ነጥብ ይዞ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ።

የሜዳ ቴኒስ 

ፖላንዳዊቷ የሜዳ ቴኒስ ምርጥ ተጨዋች ኢጋ ስዊያቴክ  የቤላሩስ ተፎካካሪዋ አሪና ሳባሌንካን ትናንት በግማሽ ፍጻሜ 6 ለ3 እና 6 ለ2 በማሸነፍ የዓለማችን ቁጥር አንድ የሜዳ ቴኒስ ተጨዋችነቷን አስመስክራለች ። ዛሬ ማታ በፍጻሜው አሜሪካዊቷ ጄሲካ ፔጉላን ትገጥማለች ። ጄሲካ ለፍጻሜ የበቃችው ሌላኛዋ አሜሪካዊት ተጋጣሚዋን ከትናንት በስትያ 6 ለ2 እና 6 ለ1 በሆነ ሰፊ የነጥብ ልዩነት በማሸነፍ ነው ።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ኂሩት መለሠ