1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
ኤኮኖሚአፍሪቃ

የውጭ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ ገበያ፣ የኤኮኖሚስቱ አስተያየት

ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 15 2016

በዚህ የመንግሥት ውሳኔ መሠረት የውጭ ባለሃብቶች ቡናና የቅባት እህሎችን ጨምሮ ሌሎች የግብርና ምርቶችን እና የቁም እንስሳትን ወደ ውጪ እንዲልኩ ፣ ከነዳጅ እና ማዳበሪያ በስተቀር በሁሉም ገቢ ንግድ ላይ እንዲሳተፉ ይፈቀድላቸዋል።

https://p.dw.com/p/4f6Ce
ባለሙያዉ እንደሚሉት የዉጪ ባለሐብቶች በኢትዮጵያ ንግድ መሳተፍ አዳዲስ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ለመክፈት ይጠቅማል
ኢትዮጵያ ዉስጥ ከተገነቡት የኢንዱስትሪ ፓርኮች አንዱ የሆነዉ የሐዋሳ እንዲሱትሪ ፓርክምስል Shewangizaw Wegayehu/DW

የውጭ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ ገበያ፣ የኤኮኖሚስቱ አስተያየት

 

የኢትዮጵያ መንግሥትየውጭ ሀገር ዜጎች በገቢ፣ በወጪ፣ በጅምላ እና በችርቻሮ ንግድ መስኮች እንዲሰማሩ መፍቀዱ "ትልቅ የቁጥጥር ተቋም ተቋቁሞ እስከተሠራበት" ድረስ በጎ እርምጃ መሆኑን አንድ የኢኮኖሚ ባለሙያ ገለፁ።

ይሁንና "ሀገሪቱ ውስጥ ያለው አለመረጋጋት" የውጭ ባለሃብቶች እድሉን እንዳይጠቀሙ ከማድረጉም በላይ አጭበርባሪ ድርጅቶች በምርት ሰበብ ሰፋፊ ቦታዎችን ተረክበው ሕገ ወጥ ድርጊት ውስጥ እንዳይገቡ ሥጋት መፍጠሩ እንደማይቀርም ተገልጿል።

በዚህ የመንግሥት ውሳኔ መሠረት የውጭ ባለሃብቶች ቡናና የቅባት እህሎችን ጨምሮ ሌሎች የግብርና ምርቶችን እና የቁም እንስሳትን ወደ ውጪ እንዲልኩ ፣ ከነዳጅ እና ማዳበሪያ በስተቀር በሁሉም ገቢ ንግድ ላይ እንዲሳተፉ ይፈቀድላቸዋል።ይህ ሁኔታ የሀገር ውስጥ ምርትን እንዳይገድብ፣ ኢትዮጵያውያን ባለሃብቶችን ከገበያ ውድድር ውጪ እንዳያደርጋቸው እና የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት እንዳይደፈጥጥ ከፍተኛ ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ ባለሙያው ተናግረዋል።//

የውጭ ባለሃብቶች በገበያ መሳተፋቸው ምን ጠቀሜታ ይኖረዋል? 

የምጣኔ ሀብት ባለሙያው ዶክተር ቆስጠንጢኖስ በርኸ የውጭ ባለሃብቶች የኢትዮጵያ ገበያ ውስጥ መግባታቸው "በተበታተነ ሁኔታ የሚመራ" ያሉትን የሀገሪቱን የግብይት ሁኔታ፤ በሕግና ሥርዓት እንዲመራ ከማድረግ ባለፈ የዋጋ መረጋጋትንም ይዞ ይመጣል። እንዴት ? 

"በየጊዜው አንድ ሁኔታ ተፈጠረ በሚል ዋጋ ዝም ብለው የሚጨምሩ አይደሉም"ኢትዮጵያ ውስጥ ይህን መሳዩ ውሳኔ እስካሁን የመቆየቱን ተገቢነት "ግራ የሚያጋባ" የሚሉት ባለሙያው በአንድ በኩል ኢትዮጵያ ውስጥ "በወጪ እና ገቢ ንግድ ላይ የተሰማሩ ሰዎች ቁጥር እጅግ ጥቂት" መሆናቸው ፣ በዚህም የሀገሪቱ የችርቻሮ እና የጅምላ ንግድ የዳበረ አለመሆኑ ለውሳኔው አሳማኝነት አስረጂ ይጠቅሳሉ።

"ከፍተኛ የኢንዱስትሪ ፓርኮች እየተስፋፉ ይመጣሉ።በሌላ በኩል አሁን እድሉ የተፈቀደላቸው የውጭ ባለሃብቶች አለም አቀፍ ልምድ፣ ሰፊ ሀብት ፣ ቀልጣጣፋና ተወዳዳር አሠራር ይዘው የሚመጡ መሆናቸው ውሳኔው በበጎ እንዲታይ የሚያደርግ ነው።

የኢትዮጵያ መገበያያ ገንዘብ። ብር
የዉጪ ባለሐብቶች ኢትዮጵያ ዉስጥ እንዲነግዱ መፈቀዱ የዉጪ ምንዛሪ ለማስገባትም ይረዳል ይባላልምስል Solomon Muchie/DW

" እንዲሁ ዝም ብሎ በጉሊት ገበያ እንኑር የሚባል ከሆነ በጣም አስቸጋሪ ነው የሚሆነው"

ለውሳኔው የቀረበው ምክንያት እና የፈጠረው ሥጋት

ለሀገር ውስጥ ባለሃብቶች ብቻ ተፈቅደው የቆዩት እነዚህ የንግድ ዘርፎች የአገልግሎት ተደራሽነት ፣ የጥራትና የብቃት ችግሮች ውስጥ ከመሆናቸው ባለፈ ለሕገ ወጥ ድርጊት መጋለጣቸው መንግሥት ይህንን ውሳኔ እንዲያሳልፍ ምክንያት ሆኖ ተጠቅሷል።

"ሀገሪቱ ውስጥ ያለው አለመረጋጋት እሱን ማሰብ ያስፈልጋል። የውጭ ኩባንያዎች እንዲህ ያለ ሁኔታ ባለበት መጥተው እንሥራ የሚሉ አይመስለኝም" 

ይህ እንዳለ ሆኖ ኢትዮጵያዊያን ከውጭ ባለሃብቶች ጋር ተወዳድሮ ገበያ ውስጥ መቆየት ፈተና እንደሚሆንባቸው በመጥቀስ፣ ሀገሪቱ የርካሽ ሸቀጦች ማራገፊያ ሆና አምራችነት እንዳይከስም ሥጋት አጭራል። የኢኮኖሚ ባለሙያው እንደሚሉት ለዚህ መፍትሔው ትልቅ የቁጥጥር ተቋም መገንባት ነው። 

ጉዳዩ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን ከማስከበር አንፃርም ሲታይ 

የኢትዮጵያ የገበያ ሁኔታ መንግሥት ስኳርን ጨምሮ "ባልተፈለገ" ባሉት ሥራ ወይም ችርቻሮ ውስጥ እንዲገባ አድርጓል የሚሉት ባለሙያው። ውሳኔው ውጤታማ እንዲሆን ከተፈለገ "የፋይናንስ ሥርዓቱ መስተካከል፣ የሙስና ቁጥጥሩ መጥበቅ እና ሥራ መስራት የሚያስችል ምቹ ሁኔታ መፈጠር ይኖርበታል።

ሰለሞን ሙጬ

ነጋሽ መሐመድ

አዜብ ታደሰ