1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኒዠር፦ የኢኮዋስ ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት ይሳካ ይሆን?

ዓርብ፣ ነሐሴ 5 2015

የምዕራብ አፍሪቃ የመከላከያ አዛዦች ሐሙስ ዕለት በናይጀሪያ ዋና ከተማ አቡጃ ላይ ተሰብስበዉ፤ የኒዠርን ፕሬዝዳንት ሞሐመድ ባዙምን ወደ ስልጣን ለመመለስ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ካልተደረገ ወይም ካልተሳካ ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት ሊኖር እንደሚችል ተወያይተዋል።

https://p.dw.com/p/4UnWV
Nigerianische Armee | Nigeria
ኤኮዋስምስል STEFAN HEUNIS/AFP/Getty Images

ኤኮዋስ ወደ ኒዠር ወታደሮች የመላክ ዕድሉ ምን ያህል እዉንስ ይሆን?

ኒዠር፦ የኢኮዋስ ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት ይሳካ ይሆን?

የምዕራብ አፍሪቃ የኤኮኖሚ ማሕበረሰብ «ECOWAS» የኒዠርን ዴሞክራሲ ለመመለስ ኃይልን የመጠቀም አቅሙ ብሎም የስኬት ዕድሉ ምን ይመስላል ይሆን?

የምዕራብ አፍሪቃ የመከላከያ አዛዦች ሐሙስ ዕለት በናይጀሪያ ዋና ከተማ አቡጃ ላይ ተሰብስበዉ፤ የኒዠርን ፕሬዝዳንት ሞሐመድ ባዙምን ወደ ስልጣን ለመመለስ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ካልተደረገ ወይም ካልተሳካ ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት ሊኖር እንደሚችል ተወያይተዋል። ባሳለፍነዉ እሁድ የምዕራብ አፍሪቃ አገሮች የኢኮኖሚ ማኅበረሰብ «ኢኮዋስ»፣ የመንግሥት ግልበጣ ያካሄዱት መኮንኖች ባዙምን ወደ ሥልጣን ካልመልሱ ኃይልን እንደሚጠቀም ዝቶ ነበር።

Pro-Putsch-Demo in Nigers Hauptstadt Niamey
የኒጀር ቀዉስምስል Djibo Issifou/dpa/picture alliance

ኤኮዋስ ወደ ኒዠር ወታደሮች የመላክ ዕድሉ ምን ያህል እዉንስ ይሆን?

የአካባቢያዊ ፖለቲካ ተንታኝ የኒዠር ተወላጁ ኦቪግዌ ኤጊጉ እንደሚሉት «ጣልቃ ገብነት የማድረጉ አጋጣሚ በጣም ከፍተኛ ነው። ምክንያቱም ለዚህ ጉዳይ ምክንያት የሚሆኑ ብዙ ነገሮች አሉ» ሲሉ ዩናይትድ ስቴትስን ጠቅሰዋል። ኤጉጉ እንደሚሉት ኒዠር ጂሃዲስቶችን ከመታገል ጋር በሚካሄደዉ ስራ የሳህል ወሳኝ አጋር በመሆንዋ ዩናይትድ ስቴትስም ኒዠርን ትፈልጋታለች፤ ብለዋል።

ከዚህ በተጨማሪም ይላሉ፤ የፖለቲካ ተንታኙ፤ በኒዠር የሚታየዉ አለመረጋጋት፤ ሩሲያን ይበልጥ ተጽዕኖ እንድታሳድር ያስችላታል። በወታደራዊ መሪዎች ያላቸዉ የአፍሪቃ መንግሥታት ለምዕራቡ ዓለም ጀርባቸውን ሲመልሱና ክሬምሊን ሲቀበሉ እየታየ ነዉ።

በሌላ በኩል የምዕራብ አፍሪቃ የኤኮኖሚ ማሕበረሰብ «ኢኮዋስ» በምዕራብ አፍሪቃ ዲሞክራሲያዊ ሽኩቻን፤ የመንግስት ግልበጣን ለመቆጣጠር ታግሏል። ባለፉት ሁለት ዓመታት በማሊ፣ በቡርኪና ፋሶ እና በጊኒ ስልጣኑንን ወታደራዊ አገዛዞች ከተቆጣጠሩ በኋላ ኤኮዋስ መፈንቅለ መንግሥትን እንደማይታገሥ ቃል ገብቶ ዝቶም ነበር።

Niger Französische Soldaten unterstützen französische Staatsangehörige auf einem Flugplatz
የኒጀር እና ፈረንሣይ ወታደሮች የፈረንሳይ ዜጎችን በአየር መንገድ ሲረዱምስል Sam Mednick/AP Photo/picture alliance

በኒዠር ታዋቂ ጋዜጠኛ እና የሳህል አካባቢዎች ተንታኝ ዛዲግ አባ እንደሚሉት በኒዠር መንግስት ግልበጣ ካካሄዶት ጋር የመደራደር ተስፋ አለ፤ ብለዉ ያምናሉ። ይሁን እና  ኢኮዋስ ወደ አማካኝ ለመምጣት የሚያደርገዉ ሙከራ ቀላል አይደልም ባይ ናቸዉ።

«አስቸጋሪ በሆነ ሁኔታ እንኳን በኒዠር ስልጣኑን በጉልበት በያዘዉ እና በወታደሩ መካከል ያለዉን ግትር አቋም የማላላት እድል ብዙ ተስፋ ሊኖር ይችላል። በኒዠር ውስጥ ስልጣኑን በተረከበዉ እና በወታደሩ መካከል ሽምግልና ሊደረግ ይችላል። ይህ የኤኮዋስን ተልዕኮ አካሄድ አቋምን የማላላት ተስፋ ሊሰጥ ይችላል»

ኢኮዋስ ምን ያህል ወታደሮች ይኖሩት ይሆን?

15 አባላት ሃገራት ያሉት ኤኮዋስ ከዚህ በፊት ተመሳሳይ ዛቻዎችን ማድረጉ አይዘነጋም።  በቅርቡ  ማለትም በ 2017 ዓመት የጋምቢያዉ የረጅም ጊዜ ገዢ ያህያ ጃሜህ፤ በምርጫ ከስልጣን መሰናበታቸዉን አልቀበልም ብለዉ ስልጣን አለቅም ባሉበት ወቅት፤ኢኮዋስ ወደ ጋምቢያ 7000 ወታደሮችን ሲልክ ያህያ ጃሜህ ስልጣኑን ለቀዉ ሃገር ጥለዉ መጥፋታቸዉ ይታወቃል።

ጋምቢያ ዉስጥ አሁንም ድረስ ከሴኔጋል፣ ከጋና፣ ከማሊ፣ ከቶጎ እና ከናይጄሪያ የተውጣጡ ወደ 2,500 የሚሆኑ የኤኮዋስ ወታደሮች በሀገሪቱ ሰላምን ለማስፈን በሚደረጉ እንቅስቃሴ ላይ ይሳተፋሉ።

ከዚህ በተጨማሪም ኢኮዋስ በጎርጎረሳዉያኑ 2022 ዓመት፤ የካቲት ወር ላይ በጊኒ ቢሳዉ የመንግሥት ግልበጣ ሙከራ ከተደረገ በኋላ አገሪቱን የሚያረጋጉ ከናይጄሪያ፣ ከሴኔጋል፣ ከአይቮሪኮስት እና ከጋና የተዉጣጡ ወደ 600 የሚጠጉ ወታደራዊ ኃይላትን አሰማርቷል።

የኢኮዋስ በኒዠር ጣልቃ የመግባት እንቅስቃሴ ምናልባትም ወደ 223,000 ወታደሮች እና ዘመናዊ ተዋጊ አውሮፕላኖች ሄሊኮፕተሮች እና ዘመናዊ የጦር መሳርያዎች ባለቤት በሆነችዉ በናይጀርያ መንግሥት ላይ ትምምን ሊኖረዉ ይገባ ይሆናል።

ናይጄሪያ በአካባቢው ላይ ግዙፍ ወታደራዊ ኃይል ያላት ከመሆኑም በላይ ከኒዠር ጋር 1,000 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለዉ የጋራ ድንበር ትቋደሳለች። 

ባለፈዉ ሐሙስ ሴኔጋል፤ ኢኮዋስ በኒዠር ወታደራዊ ጣልቃ መግባቱን ከወሰነ እሳተፋለሁ ስትል ዝግጁነትዋን ገልጻለች። ይሁን እና በርካታ የኢኮዋስ አባል አገራት በኒዠር የኃይል እርምጃን እንደማይደግፉ አስቀድመው ተናግረዋል ።

የኒዠር ፖለቲካ ተንታኝ አብዱል ሙሙኒ አባስ እንደሚሉት ከናይጀሪያ ጎረቤታችን ሌላ ሞሪታኒያ እና አልጄሪያ ወደ ኒዠር መዝመትን አይስማሙም ብለዋል።  ማሊና ቡርኪፋሶም ይህን አይደግፉም። ቤኒንም ቢሆን ኒዠርን አያጠቃም፤ ሲሉ አክለዋል። የናይጄሪያ ጦር በገዛ ሃገሪቱ ከሚገኙ  36 ግዛቶች ውስጥ በ30  ግዛቶች ቦኮ ሃራምን እና የታጠቁ ሽፍቶችን በመዋጋት በራሱ ችግር ተጠምዶ ነዉ የሚገኘዉ።  

Nigeria Abuja | ECOWAS-Treffen zur Lage in Niger
ናይጀርያ አቡጃ ላይ የተገናኙት የኤኮዋስ ከፍተኛ መኮንኖች ምስል KOLA SULAIMON/AFP

በኒዠር ታዋቂ ጋዜጠኛ እና የሳህል አካባቢዎች ተንታኝ ዛዲግ አባ እንደሚሉት የኒጀሩ ወታደራዊ ኃይል እጅ ላለመስጠት ቁርጠኛ ነዉ። «ለኒዠር መፈንቅለ መንግስት ኃላፊ የሆነው ወታደሩ እጅ ላለመስጠት ቁርጠኛ ነው። የገለበጡበትን አገዛዝ የመመለስ ጥያቄንም ፈጽሞ አይቀበልም። ነገር ግን በአቋም ደረጃ  ወደ መካከለኛ አቅጣጫ ሊመጡ ይችሉ ይሆናል። ለምሳሌ ሽግግሩን አብሮ የማስተዳደር ጥያቄ፣ ወይም የአጭር የሽግግር የስልጣን ጊዜ ጥያቄ ወይም የሲቪል መንግስት ሹመትን ይጠይቁ ይሆናል።»

ኒዠር በሳህል እምብርት ላይ የምትገኝ ሰፊ አገር ናት። ምንም እንኳ ከዓለም ድሃ አገሮች አንዷ ብትሆንም፣ ወታደሮቿ ከጂሃዲስቶች ጋር የመዋጋት ልምድ ያላቸዉ ናቸዉ። በአገሪቱ ውስጥ ዩናይትድ ስቴትስ 1,100 ወታደሮች ፤ ፈረንሳይ ደግሞ ወደ 1,500 ገደማ ሠራዊቶቻቸዉን አስፍረዉ ይገኛሉ።

አዜብ ታደሰ / ኬት ዎከር

ሸዋዬ ለገሠ