1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የደቡብ ሱዳን የሥልጣን ሽኩቻ መዘዝ፣

ዓርብ፣ ታኅሣሥ 11 2006

የሰሜን ሱዳን የፖለቲካ ተጽእኖና ፤ የዐረብ ባህል ጫና አንገሽግሾት 22 ዓመታት መሪር ትግል ያካሄደው የደቡብ ሱዳን ህዝብ፤ ነጻነት ባወጀ በ 2 ዓመት ከመንፈቅ ገደማ ወደ አስከፊ የእርስ በርስ ውጊያ እንዳያመራ አሥግቷል። ባለፈው እሁድ በመዲናይቱ

https://p.dw.com/p/1AeIP
ምስል Reuters

በጁባ ያገረሸው ውጊያ ፣ የ 500 ያህል ሰዎችን ሕይወት ቀጥፎ ፤ 34,000 ሰዎች፤ በተባበሩት መንግሥታት ጣቢያዎች መጠለያ እንዲሻ አስገድዷል ። የሥልጣን መቀናቀን ነው የተባለለት ውዝግብ ፣ በጎሣ ልዩነት ተካሮ ባፋጣኝ ወደሌሎች አካባቢዎች መዛመቱ የሚታወስ ነው። ጉዳዩ ያሳሰባቸው የምሥራቅ አፍሪቃ በይነ መንግሥታት ሚንስትሮች ፤ የአፍሪቃ ኅብረትና የተባበሩት መንግሥታት ተወካዮች ጁባ ውስጥ ከሀገሪቱ ፕሬዚዳንት ሳልባ ኪር ጋር በዛሬው ዕለት እንደሚወያዩ ይጠበቃል። ስለደቡብ ሱዳን ወቅታዊ ይዞታ ፣ በፀጥታ ጉዳይ ተቋም፤ (ISS)የምሥራቅ አፍሪቃ ፖለቲካ ጉዳዮች ተንታኝ በማነጋገር የተጠናቀረው ዘገባ የሚከተለው ነው።

Südsudan Riek Machar Vizepräsident Archiv 2011
ምስል Stan Honda/AFP/Getty Images

ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር ባለፈው ዓመት በሐምሌ ወር ምክትላቸውን ሪኤክ ማቻርን ከስልጣን ካሰናበቱ ወዲህ ቁርሾው አይሎ፣ የሥልጣን ሽኩቻው ባለፈው እሁድ መፈንዳቱ የሚታወስ ነው። የጎሣ ልዩነትን ብቻ መሠረት ባደረገ በዚያ የተኩስ ልውውጥም ሆነ የኃይል እርምጃ፤ ብዙ ሰዎች ያላበሳቸው የጥይት ራት የሆኑበት ድርጊት የተባበሩትን መንግሥታት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ኀላፊ ናቪ ፒላይን እጅግ እንዳሳዘነ ተመልክቷል። ራሳቸው የተ መ ድ ዋና ጸሐፊ ባን ኪ ሙን፤ በበኩላቸው ፣ ውዝግቡ ባስቸኳይ በፖለቲካ ውይይት መላ እንዲፈለግለት ነው ያስገነዘቡት።

Südsudan Süd Sudan Flüchtlinge Unruhen Juba
ምስል Reuters

አንዳንድ የ ምሥራቅ አፍሪቃ በይነ መንግሥታት (IGAD) አባል ሃገራት ውዝግቡን በቀላል ሊፈታ እንደሚችል በተስፋ ይሁን ዲፕሎማሲያዊ ፈሊጥ አድርገው ያን ያህል የሚያሳስብ እንዳልሆን መግለጫ ቢሰጡም፤ ተጨባጩ ይዞታ የሚያረጋጋ ሆኖ አልተገኘም። አንዳንድ መንግሥታት ዜጎቻቸውን ለማስወጣት አኤሮፕላኖች ን በመላክ ላይ ናቸው። አሶኬ ሙከርጂ የተባሉት ህንዳዊ የተባበሩት መንግሥታት ልዑክ፤ 3 ህንዳውያን ሰላም አስከባሪዎች፤ ሆን ተብሎ የጥይት ዓላማዎች መሆናቸውን ተናግረዋል። ዩጋንዳ ዜጎቼን ለመጠበቅ ነው በሚል ሰበብና ከጁባ መንግሥትም ጥሪ ቀርቦልኝ ነው በማለት ፤ በዛሬው ዕለት በደቡብ ሱዳን መዲና ጦር ሠራዊት አሠማርታለች። ትናንት ብርቱ ማስጠንቀቂያ ያሰሙት የዩናይትድ እስቴትሱ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፣ 45 ወታደሮቻቸው እንዲሠማሩ አድርገዋል። የዚህ ያልተጠበቀ መስሎ የቆየው ውዝግብ ፍንዳታ ዋና መንስዔው ምን ይሆን? ዋና ጽ/ቤቱ በፕሪቶሪያ ፤ ደቡብ አፍሪቃ በሚገኘው የፀጥታ ጉዳይ ተቋም ፣ የምሥራቅ አፍሪቃ የፖለቲካ ጉዳዮች ተንታኝ አንድርውስ አታ አሳሞዋ--

\ «ጉዳዩን ሰፋ አድርገን ካየነው፣ በፕሬዚዳንቱ ክብር ዘብ የተፈጠረ ምሥቅልቅል፤ የአገሪቱን የፖለቲካ ክፍፍል አሥፍቶታል። የጎሣ ልዩነትም እንዲጎን ነው ያደረገው። ቀስ በቀስምየጎሳ ልዩነትን በማባባስ፣ በፖለቲካው አመራር ለረጅም ጊዜ የቆየውን ክፍፍል በጦር ሠራዊቱና በብሔረሰቦችም ዘንድ ጥርጣሬውን ያባብሰዋል። ይህ ደግሞ፣ አገሪቱ ነጻነት ከማወጇ በፊት አንስቶ ብዙዎች ሲፈሩት የነበረውን ውዝግብ እውን ሊያደርገው በቅቷል።»

Südsudan Juba Ausschreitungen Krankenhaus Patienten
ምስል Reuters

ደቡብ ሱዳን እ ጎ አ ከ 1983-2005 ባካሄደችው የ 22 ዓመታት መሪር የትጥቅ ትግል ከ 2 ሚሊዮን በላይ ተወላጆቿን እንዳጣች ነው ታሪኳ የሚያስረዳው። ስለሆነም ሰፊ መስዋእትነት የከፈለ ህዝብ አሁን እርስ በርስ እንዳይፋጅ ያሠጋበት አደጋ ስለመኖሩ በሚነገርበት ወቅት ውዝግቡ በቀላል እንደሚፈታ መገመት ይቻላል?

«ሳልቫ ኪርንና ሪኤክ ማቻርን ወደ ጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት ማምጣቱ ከሞላ ጎደል ቀላል ሊሆን ይችላል። ይህ ግን ሁለቱን የፖለቲካ መሪዎች ወይም ተቀናቃኞች የሚመለከት ነው። ግን ፤ ጉዳዩ የዲንካና የኑኤር መቀናቀን መሆኑ ሊዘነጋ አይገባም። በፖለቲካው መስክ በከፍተኛ አመራር ላይ ባሉት ቅራኔውን እንደምንም ማርገብ ቢቻል እንኳ በሀገሪቱ በመላ ሲብላላ የቆየው ችግር እንደምናስበው በቀላሉ ሊወገድ የሚችል አይደለም።»

የደቡብ ሱዳንን ውዝግብ፣ የካርቱምን መንግሥት በጥሞና ነው የሚመለከተው። በአንድ በኩል ከደቡብ ሱዳን መንግሥት ጋር የሚወያዩባቸው አንዳንድ ዐበይት የጋራ ጉዳዮች በአንጥልጥል እንዲቀሩ አይሻም። በሌላ በኩል የካርቱም መንግሥት ለአፈንጋጩ ሪኤክ ማቻር ሊያደላም ሆነ ሊደግፍ እንደሚችል የሚናገሩ አሉ። በደቡብ ሱዳን የተፈጠረው ውዝግብ እንዲወገድ ተጽእኖ በማድረግም ሆነ በመሸምገል መፍትኄ ሊያፈላልጉ የሚችሉ አገሮች ን መጥቀስ ያቻላል?

Südsudan Juba Ausschreitungen Verletzte 17.12.2013
ምስል Reuters

«የአካባቢው አገሮች፤ ዩጋናዳ ኬንያና ኢትዮጵያ ጁባን በሰፊው ማግባባት የሚችሉ ናቸው። ጎረቤቶች ስለሆኑ ብጻቻ አይደለም። ሰሙኑን ሳያገልሉ፣ በጦርነቱ ወቅት የተጫውቱት ሚና እጅግ ከፍ ያለ ነው። ደቡብ ሱዳን ለአነዚህ አገሮች ዐቢይ ከበሬታ ነው ያላት። ብዙዎች ደቡብ ሱዳናውያን፤ ኬንያን በአስተናጋጅነቷ ብቻ ሳይሆን ፤ ብዙ የሚያቀራርቧቸው ጉዳዮች እንዳሉም ይሰማቸዋል። ያም ሆነ ይህ «ኢጋድ» በመሪነት መላ ቢሻ በጣም ጥሩ ነው፤ ይሁንና ዩጋንዳን የመሳሰሉ አገሮችም ለደቡብ ሱዳን መልሶ ሰላም ለማስገኘት በከፍተኛ ደረጃ ተሰሚነት ያላቸው መሆኑ ሊዘነጋ አይገባም።»

ተክሌ የኋላ

ሸዋዬ ለገሠ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ