1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፍሪቃ የልማት ባንክ አዲስ ፕሬዚደንት መምረጡ

ማክሰኞ፣ ግንቦት 25 2007

የአፍሪቃ የልማት ባንክ ባለፈው ሀሙስ ዋና ጽሕፈት ቤቱ በሚገኝባት በኮት ዲቫር የአቢዦ ከተማ ባካሄደው ስብሰባ ላይ አዲስ ፕሬዚደንት መረጠ። ዘንድሮ 50ኛ ዓመቱን የያዘው ይኸው ባንክ በአህጉሩ ድህነትን ለመታገል እና የአህጉሩን ሕዝቦች ኑሮ ለማሻሻሉ ተግባር ትኩረት ሰጥቶ ተንቀሳቅሶዋል።

https://p.dw.com/p/1FZE8
Logo der African Development Bank Group
ምስል ADB

[No title]

የፊታችን እአአ ነሀሴ 31 የሚሰናበቱትን የአፍሪቃ ልማት ባንክ ፕሬዚደንት ርዋንዳዊ ዶክተር ዶናልድ ካቤሩካን ለመተካት በኮት ዲቯር የአቢዦ ከተማ በተደረገው ምርጫ ላይ ናይጀሪያ፣ ኢትዮጵያ፣ ኬፕ ቬርዴ፣ ቱኒዝያ፣ ቻድ፣ ሲየራ ልዮን ፣ ዚምባብዌ እና ማሊ ዕጩዎቻቸውን አቅርበው ነበር። ከቀረቡት ስምንት ዕጩዎች መካከል ሶስቱ ፣ ብሎም ናይጀሪያዊው የግብርና ሚንስትር አኪንዉሚ አዴሴኔ፣ የኢትዮጵያ ፋይናንስ እና የኤኮኖሚ ልማት ሚንስትር አቶ ሱፍያን አህመድ እና ብቸኛዋ ሴት ተወዳዳሪ የኬፕ ቬርዴ የፋይናንስ ሚንስትር ክሪስቲና ዱዋርቴ ከፍተኛ የማሸነፍ ዕድል እንደነበራቸው የስብሰባውን የተከታተሉት ተንታኞች ገምተው ነበር። ዶይቸ ቬለ በአቢዦ ያነጋገራቸው ለንደን የሚገኘው « አይ ሲ ፓብሊኬሽን » የተባለው የአሳታሚ ድርጅት ኃላፊ እና የምጣኔ ሀብት ባለሙያ ኦማር ቤን የደር ባንኩ የአህጉሩን ምጣኔ ሀብት የሚያራምድ ፕሬዚደንት እንደሚያስፈልገው ነው የገለጹት።

Donald Kaberuka, Präsident der Afrikanischen Entwicklungsbank ADB
ዶናልድ ካቤሩካምስል AFP/Getty Images/S. Kambou

« የተጠቀሱት ዕጩዎች በጠቅላላ በጣም ችሎታ ያላቸው ናቸው። ለምሳሌ፣ የኢትዮጵያ ፋይናንስ ሚንስትር ባለችሎታ ናቸው፣ እንደሚታወቀው፣ ኢትዮጵያ በአፍሪቃ ፋጣን ዕድገት ካሳዩት ሀገራት መካከል አንዷ ናት። የኬፕ ቬርዴዋ ክሪስቲ ዱዋርቴም ከፍተኛ ችሎታ አላቸው። እና አንዱ ዕጩ ከሌላኛው በነዚህ ወይም በሌሎች ጉዳዮች ይበልጣል ብሎ መናገር አይቻልም። ስለዚህ ባንኩ የሚመርጠው መሪ ባሁኑ ጊዜ የተጀመረውን ተሀድሶ የሚቀጥል፣ በዓለም አቀፍ ደረጃም የአህጉሩ የኤኮኖሚ ልማት መሻሻል ድምፅን የሚያስተጋባ መሆን አለበት። »

ከስድስት የምርጫ ሂደት በኋላ የ55 ዓመቱ ተሰናባቹ ናይጀሪያዊው የግብርና ሚንስትር አኪንዉሚ አዴሴኒ የቀናቸው ሲሆን፣ ባለፉት 10 ዓመታት ባንኩን ያስተዳደሩትን ዶናልድ ካቤሩካን ይተካሉ። እንደ ኤኮኖሚ ባለሙያው ኦማር ቤን የደር አስተያየት፣ ካቤሩካ አበረታቺ ሁኔታ ላይ የሚገን ባንክ ነው ለተከታያቸው የሚያስተላልፉት። የአፍሪቃ የልማት ባንክ በያመቱ በአህጉሩ ከበጀቱ መካከል ከግማሽ የሚበልጠውን፣ ማለትም፣ ወደ ሁለት ቢልዮን ዶላር የሚጠጋ ብድር በመስጠት በአህጉሩ ልማት መሻሻል ላይ ትልቅ ድርሻ ያበረከተ ተቋም መሆኑን ኦማር ቤን የደር አስረድተው፣ ይህ ገሀድ ለሥዩሙ የባንክ ፕሬዚደንት አክዉሚኒ አዴሴኒ አዎንታዊ ሁኔታ እንዳመቻቸ ጠቁመዋል።

Akinwumi Adesina, neuer Präsident der Afrikanischen Entwicklungsbank
አኪንዉሚ አዴሴኒምስል AFP/Getty Images/S. Kambou

« የተመረጠው ሰው ጠንካራ ተቋም የሚረከብ ይመስለኛል። ስለማንኛውም ግዙፍ አፍሪቃዊ የመሠረተ ልማት ፕሮዤ መረጃ ለሚፈልግ ሁሉ፣ ወይም፣ የአቅም ግንባታን ለመሳሰሉ ዓበይት ጥያቄዎች መፍትሔ ወይም መልስ በማፈላለጉ አኳያ ባንኩ እንደ አማራጭ ድርጅት የሚታይ ነው። ባንኩ ዓቢዩን ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ቀውስን የተቋቋመ ወይም ለፀረ ኤቦላ ወረርሽኙ ትግል ባፋጣኝ ድጋፍ የሰጠ የመጀመሪያው ባንክም ነበር። በዓለም አቀፍ ደረጃ የፋይናንሱ ቀውስ ቢከሰትም ካቤሩካ ባንኩን የማጠናከር እና አስተዳደሩን ከማዕከላይ እዝ የማላቀቁ ተግባር ተሳክቶላቸዋል። በወቅቱ ባንኩ 25 ያካባቢ ጽህፈት ቤቶች ከፍቶ በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል። »

የአፍሪቃ የልማት ባንክ የሰጠውን ብድር የአህጉሩን መሠረተ ልማት፣ በተለይ የኃይሉን ምንጭ እና የትራንስፖርቱን ዘርፍ ሻሻያው በማዋል እአአ ከ2005 ዓም ወዲህ ባንኩን ያስተዳደሩት ዶናልድ ካቤሩካ ካቤሩካ ጥሩ ውጤት በማስመዝገብ ሰፊ ድርሻ ማበርከታቸውን ኦማር ቤን የደር ገልጸዋል።

« ካቤሩካ ከርሳቸው በፊት ከነበሩት የሞሮኮ ኦማር ካባዥ በተረከቡት ግዙፍ የመሻሻል ተስፋ በነበረውን ባንክ አሰራር ላይ ተሀድሶ በማድረግ ተጨባጭ ውጤት ማስገኘት ተሳክቶላቸዋል። እርግጥ ፣ የአፍሪቃ የልማት ባንክ እንከን አልባ ድርጅት አይደለም። ብዙ መሻሻል ይኖርበታል። ለምሳሌ በብድር አሰጣጡ ወይም ፕሮዤዎችን በመቀበሉ ውሳኔ ሂደት ላይ ፈጣን ሊሆን ይገባዋል። ባጠቃላይ ሲታይ ግን የባንኩ አሰራር በጣም ጥሩ ነበር። »

ሥዩሙ ፕሬዚደንት ናይጀሪያዊው አኪንዉሚ አዴሴኒ በባንኩ የተሀድሶውን ርምጃ አጠናክረው የመቀጠል እና የመtረተ ልማት ፕሮዤዎችን በማፋጠኑ ርምጃ ላይ የባንኩን አሰራር ይበልጥ የማነቃቃት ትልቅ ተግባር እንደሚጠብቃቸው ከወዲሁ ተገልጾዋል።

አርያም ተክሌ

ልደት አበበ