1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአውሮፓ ህብረት የተገን አሰጣጥ መርህ

ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 1 2005

ከ 2 ሳምንት በፊት ብራሰልስ ውስጥ በጉዳዩ ላይ የተነጋገሩት የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት ተወካዮችና የሃገር ውስጥ ጉዳዮች ኮሚሽነር ሴሲሊያ ማልምስቶርም የጋራ የተገን አሰጣጥ የስደተኞች አያያዝ ረቂቅ ደንቦች ላይ ተስማምተዋል ።

https://p.dw.com/p/18Chd
ምስል picture-alliance/Milestone Media

የአውሮፓ ህብረት ፣ ስደተኞች ወደ አባል ሃገራት እንዲዳይገቡ ለመከላከል ፣ ድንበሩን ከመጠበቅ ባሻገር ወደ አውሮፓ መሸጋገሪያ በሆኑ ሃገራት ላይ የሚያሳድረው ተፅዕኖ እየተተቸ ነው ። የመብት ተሟጋቾች እንደሚሉት ስደተኞች ወደ አውሮፓ እንዳይገቡ ለመከላከል ህብረቱ ከአንዳንድ የሰሜን አፍሪቃ ሃገራት ጋራ በደረሰባቸው ስምምነቶች ምክንያት ስደተኞች ለሰብአዊ መብቶች ጥሰት ተዳርገዋል ።

የአውሮፓ ህብረት ፣ ለአመታት ሲያነጋግር የቆየውን በአባል ሃገራት በሙሉ ሥራ ላይ የሚውል የጋራ የተገን ጠያቂዎች አቀባበል ረቂቅ ደንብ ወደ ማፅደቁ የመቃረቡ ተስፋ መኖሩ እየተነገረ ነው ። ከ 2 ሳምንት በፊት ብራሰልስ ውስጥ በጉዳዩ ላይ የተነጋገሩት የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት ተወካዮችና የሃገር ውስጥ ጉዳዮች ኮሚሽነር ሴሲሊያ ማልምስቶርም የጋራ የተገን አሰጣጥ የስደተኞች አያያዝ ረቂቅ ደንቦች ላይ ተስማምተዋል ። እጎአ በ1990 ዎቹ መጀመሪያ ከክሮኤሽያና ከቦስኒያ እንዲሁም በ1990ዎቹ መጨረሻ ደግሞ ከኮሶቮ ስደተኞች በብዛት ወደ አውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት መጉረፍ መጀመራቸው ህዝቡን አማሮ መንግሥታትም በራቸውን ለስደተኞች ይበልጥ እንዲያጠቡ ምክንያት ሆኗል ። ከጥቂት አመታት ወዲህ ደግሞ ህብረቱ ስደተኞቹን በሩቁ ለመከላከል ከአውሮፓ በስተደቡብ ከሚገኙ ሃገራት ጋር የትብብር እርምጃዎችን እየወሰደ ነው። ከነዚህም ውስጥ በሜዴትራኒያን ባህር በኩል ወደ አውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት ለመግባት የሚሞክሩ ስደተኞችን ወደ ህብረቱ መሸጋገሪያነት ከሚያገለግሉ የሰሜን አፍሪቃ ሃገራት እንዳያልፉ ማድረግ ይገኝበታል ። በዚህ በኩል እንደ ቱኒዝያ ያሉ ሃገራት ከአውሮፓ ህብረት ጋር በደረሱባቸው ስምምነቶች ስደተኞቹ ወደ አውሮፓ እንዳይሻገሩ

Bildergalerie Lampedusa Frühling
ምስል Gaia Anderson

እየተከላከሉ ነው ። በአንዳንድ የሰሜን አፍሪቃ ሃገራት የሚገኙ የስደተኞች መብት ተሟጋቾች ህብረቱ ስደተኞች በሌላ 3 ተኛ ሃገር እንዲቀሩ ማድረጉ አሳሳቢ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን ማስከተሉን በቅርቡ ቱኒዝያ ዋና ከተማ ቱኒስ ውስጥ በተካሄደው የአለም ማህበራዊ መድረክ ላይ አስታውቀዋል ። ቱኒዝያን የመሳሰሉ የሰሜን አፍሪቃ ሃገራት ፣ ወደ አውሮፓ ለመሻገር አልመው ወደ እነዚህ ሃገራት በሚመጡ ህገ ወጥ በሚባሉ ስደተኞች ላይ እርምጃ የሚያስወስዳቸው የጋራ ስምምነቶች ተግባራዊ እያደረጉ ነው ። እነዚህ እርምጃዎችም የስደተኞች መብት ተሟጋቾቹ እንደሚሉት የሰብዓዊ መብት ጥሰት ችግሮች ዋነኛ መንስኤ ሆነዋል ። ከሞሪቴኒያ የሰብዓዊ መብቶች ማህበር አማዱ ምቦው በአውሮፓ ህብረት የስደት ጉዳይ መርህ ምክንያት የሰዎች በነፃነት የመዘዋወር መብት እየተጣሰ ነው ይላሉ ።

«ይህ እርምጃ የሰብአዊነትን ፅንሰ ሃሳብ ምንነት በጥያቄ የሚያስነሳ ነው።በሰብአዊነት በአንድ ዓይን የምንታይ ወይንስ የተለያየ የሰብአዊ መብት ያለን ተለያይተን የምንታይ ሰዎች ነን ? በአካባቢያችን በነፃነት የመንቀሳቀስ መብቱ ስለሌለን እንድናድግ ትረዱን ዘንድ እንፈልጋለን ፤»

ምቦው እንደሚሉት በተለይ ከሜዴትራኒያን ባህር በስተደቡብ ለሚመጡ ስደተኞች ሁኔታው የከፋ ነው ። ለአውሮፓውያን በነፃ የመዘዋውር መብት የሚሰጠው ህብረቱ ፣ እንደ ምቦው ስደተኞችን ግን በእኩል ዓይን አያይም ። መንግሥታዊ ያልሆነው የጀርመኑ ፕሮ አዙል የተባለው ድርጅት ባልደረባ ጁዲት ኩፕ በምቦው አስተያየት ይስማማሉ። ኩፕ የአውሮፓ ህብረት የስደተኞች መርህ በ 3 ተኛ የስደተኛ ተቀባይ ሃገር በሚያሳድረው ተፅዕኖ ላይ ጥናት አካሂደዋል ። በዚሁ ጥናታቸው የአውሮፓ የስደተኞች መርህ የአፍሪቃ ሃገራት ድንበራቸውን በጥብቅ እንዲቆጣጠሩ ማድረጉን አረጋግጠዋል ። ከዚህ ሌላ ሃገራቱ ከህብረቱ ጋር የደረሱባቸውን ስምምነቶች ተፈፃሚ ለማድረግ ስደተኞችን እያሰሩም ነው ። በዚህ ሂደት ደግሞ ወደ አውሮፓ ለመሄድ የማይፈልጉ የውጭ ዜጎች ሳይቀሩ የችግሩ ሰለባ ሆነዋል ።

Flüchtlinge Boot
ምስል picture-alliance/dpa

« በሞሪቴንያ በአጠቃላይ ስደተኞች በሙሉ ወደ አውሮፓ ለመሄድ ይሞክራሉ የሚል ጥርጣሬ አለ ። ከሃገር የመውጣት ሃሳቡ የሌላቸው ስደተኞች ሳይቀሩ ለእሥር እየተዳረጉ ነው ። እነዚህ እሥር ቤቶች ደግሞ አደገኛ ናቸው ።»

በአብዛኛዎቹ የአፍሪቃ ሃገራት ተገን ጠያቂዎችን የተመለከቱ በቂ ደንቦች የሉም ። ይህን ክፍተት ለመሙላትም የአውሮፓ ህብረት የተለያዩ እገዛዎችን በማድረግ ላይ ይገኛል ። ለምሳሌ የቱኒዝያ የሽግግር መንግሥት በአውሮፓ ህብረት እገዛ ከአዲሱ የህብረቱ የስደተኞች አቀባበል ውል ጋር የሚጣጣም መርህ እያዘጋጀ ነው ። ኮፕ የአውሮፓ ህብረት አንድ ዓለም ዓቀፍ የጀርመን ድርጅትን በመጠቀም የሜዴትራንያን ባህር በሚያዋስናቸው ሃገራት የተገን አሰጣጥ መርህ ላይ ጫና እያደረገ ነው ይላሉ ። በርሳቸው አባባል ተፅእኖው በቱኒዝያ ሉዓላዊነትም ላይ ጭምርም ነው ።

« የአውሮፓ ህብረት በገንዘብ የሚደግፋቸው የፈላስያን አያያዝና የልማት ማዕከል ICMPD ንየመሳሰሉ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች አሉ ። የቱኒዝያ መንግሥት የፍልሰት ጉዳይ ህጉን መለወጥ ይኖርበታል ። ይህም ሲሆን በዚህ በነዚህ ሃገሮች ብሔራዊ ሉዓላዊነት ላይ ሰፊ ተፅዕኖ ያሳድራል ።»

ከቱኒዝያ የስደትና የተገን ጉዳዮች ማዕከል ሃሰን ቡባክሪ እንዳሉት ደግሞ የአውሮፓ የስደተኞች ጉዳይ መርህ ከዛሬ 2 አመት በፊት ከተካሄደው የቱኒዝያ ህዝባዊ አመፅ በኋላም ሳይቀየር እንደ ቀድሞው ነው የቀጠለው ። ሃገሪቱ ከአውሮፓ የልማት እርዳታ የምታገኘውም ህገ ወጥ ፍልሰትን ለመግታት የምታደርገው ጥረት እየታየ ነው ይላሉ ቡባክሪ

« ህገ ወጥ ፍልሰትን ለመግታት መታገሉ ማለትም ወሰኖችን መቆጣጠሩ የአውሮፓ ህብረት የልማት እርዳታ ለመስጠትና ማንኛውንም ትብብር ለማድረግ ያስቀመጠው ቅድመ ግዴታ ነው »

Afrikanische Migranten Immigranten illegale Einwanderer Italien
ምስል AP

የአውሮፓ ህብረት አባል ሃገራት በቅርቡ የጋራ የተገን አሰጣጥ ና የስደተኞች አያያዝ ደንቦችን ያጸድቃሎ ተብሎ ይጠበቃል ። አባል ሃገራት በነዚህ ደንብ ውስጥ መካተት በሚገባቸው ፣ የተገን አሰጣጥ ሂደት በሚወስደው ጊዜ እና አተገባበሩ ፣ ለተገን ጠያቂዎች በሚሰጥ የገንዘብ ድጋፍ መጠን ፣ ጥገኝነት ሊያሰጡ በሚያስችሉ ሁኔታዎች እንዲሁም ስደተኞች ስለሚባረሩባቸው ደንቦች ሲነጋገሩ ና ሲከራከሩ 14 ዓመታት አልፈዋል ። ከ 2 ሳምንት በፊት የህብረቱ አባል ሃገራት ተወካዮችና የህብረቱ ኮሚሽን የተስማሙበት ረቂቅ የህብረቱ ኮሚሽን እንደሚለው የተገን ጠያቂዎች ማመልከቻዎች በትክክል በፍጥነትና በተሻለ መንገድ ውሳኔ እንዲሰጥባቸው የሚያግዝ ይሆናል ። የስደተኞች መብቶች ተሟጋች ድርጅቱ ፕሮ አዙል ግን የጋራው ደንብ በጎ ጎኖች እንዳሉት ሁሉ መጥፎ ጎኖችም አሉት ሲል አስተያየቱን ሰንዝሯል ። ከነዚህ አንዱ በወደፊቱ የተገን ጠያቂዎች አቀባበል መመሪያ መሠረት የተገን ጠያቂዎችን ማንነት ለማወቅ ፣ አንድ ሃገር የመግባት መብታቸውን ለመመርመር ወይም ከሃገራቸው ስለወጡበት ምክንያት ማስረጃ ለማሰባሰብ ተገን ጠያቂዎች በቁጥጥር ሥር እንዲቆዩ የሚደረግበት መመሪያ ይገኝበታል ። በዚሁ መመሪያ መሠረት ተገን ጠያቂዎች ማመልከቻው ዘግይተው ካስገቡ እንዲሁም ለአገር ደህንነት ያሰጋሉ ተብለው ከተጠረጠሩ ሊታሰሩ ይችላሉ ። ለተገን ጠያቂዎች መብት የሚታገለው ፕሮ አዙል የተባለው ድርጅት ባልደረባ ካርል ኮፕ በቅርብ ጊዜ ይፀድቃል ተብሎ የሚጠበቀው ረቂቅ ደንብ ወደፊት ብዙ ተገንጠያቂዎች እንዲታሰሩ ሊያደርግ ይችላል የሚል ስጋት እንዳላቸው አስታውቀዋል ።

« የተገን አጠያየቅን ሂደት በተመለከተ የማህበራዊ ኑሮ ይዞታን ያገናዘቡ መመሪያዎች በቅርብ ጊዜ ይወጣሉ ። ተገን ጠያቂን በቁጥጥር ሥር ለማዋል 6 ምክንያቶች ተዘርዝረዋል ። አንድ ተገን ጠያቂው ከሆነ አገር ሲገባ ወይም አንድ ሃገር ወደ ሌላ የአውሮፓ ህብረት ሃገር ሃላፊነቱ አይመለከተኝም ብሎ ሲያሰናብተው ለህብረተሰቡ ደህንነት አስጊ ሆኖ ከታሰበና ይህንንም የፀጥታ ይዞታ ግምት ውስጥ በማስገባት ማንነቱን አጣርቶ ለማወቅ ና የመሳሰሉት ። በሌላ አባባል አውሮፓ ሰዎች እየተያዙ የሚታሰሩበትን ደረጃውን ያልጠበቀ አሠራር አሁን ህጋዊ ለማድረግ ተነሳስቷል ። ያ ማለት ቀደም ካለው ጊዜ ይልቅ ሁን በርካታ ተገን ጠያቂዎች በእስር የሚቆዩበት ሁኔታ ይፈጠራል ። »

Illegale Einwanderer Auffanglager Italien Einwanderungszentrum in Agrigento Flash-Galerie
ምስል picture-alliance/dpa

ኮፕ የተቃወሟቸው ተገን ጠያቂዎች በቁጥጥር ሥር የሚውሉባቸው 6 ምክንያቶች አንደኛ የተገን ጠያቂውን ማንነት ለማጣራት ፣ ሁለተኛ ዓለም አቀፍ ከለላ እንዲሰጠው ወይም እንዲሰጣት ያስገባው ያስገባችው ማመልከቻ ያየዛቸውን ጉዳዮች ለማጣራት ፣ ወደ አንድ አባል ሃገር ግዛት የመግባት መብት ላይ ውሳኔ ለመስጠት ብሄራዊ ፀጥታንና ስርዓትን ለማስጠበቅ ፣ ተገን ጠያቂው ዓለም አቀፍ ጥበቃ እንዲደረግለት ያመለከተው ወደ ሃገሩ እንዳይመለስ ለማዘግየት አሰቦ ነው ተብሎ ከታመነበት ወደ ሃገሩ እንዲመለስ ዝግጅት ለማድረግ 6 ተኛ በደብሊኑ ስምምነት መሠረት ተገን ጠያቂውን ወደ ሌላ የህብረቱ አባል አገር ማስተላለፍ ሲያስፈግል ናቸው ። የፊታችን ግንቦት ወይም ሰኔ የአውሮፓ ህብረት ሚኒስትሮችና የአውሮፓ ህብረት ያጸድቋቸዋል ተብለው የሚጠበቀው ረቂቅ ደንብ የ 2003 ቱ የደብሊኑ የአውሮፓ ህብረት የተገን አሰጣጥ ደንብ ማሻሻያ ነው ።

ሂሩት መለሰ

ሸዋዬ ለገሠ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ