1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአባይ ግድብ፤ ኢትዮጵያና ግብፅ

ሐሙስ፣ ግንቦት 29 2005

የግንባታዉ ተግባር የዉሃዉን ፍሰት የሚጎዳ ከሆነ ግብፅ ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ የጀመረችዉን የግድብ ግንባታ እንድታቆም እንደምትጠይቅ የፕሬዝደንቱ አማካሪ አስታወቁ።

https://p.dw.com/p/18lJq
ምስል William Lloyd-George/AFP/Getty Images

የኢትዮጵያ መንግስት የአባይን ዉሃ ለኃይል ማመንጫ ወደሚሠራዉ ግድብ መቀልበስ መጀመሩን በመንግስት ቴሌቪዥን ይፋ ካደረገ ወዲህ ጉዳዩ የግብፅ ፖለቲከኞችና የመገናኛ ብዙሃንን ትኩረት ስቧል። ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ የጀመረችዉ የግድብ ሥራ የወንዙ ፍሰት ሊቀንስ ይችላል የሚለዉ ስጋት የተፋሰሱን ሃገራት በተለይም ግብፅን ማነጋገሩ ቀጥሏል። ሰሞኑን ከካይሮ የሚወጡ የዜና ወኪል ዘገባዎች ኢትዮጵያ የግድቡን ተግባር በዉዴታ እንድታቆም ካልሆነም ተግባሯን እንድትገታ የተለያዩ ስልቶችን የግብፅ ፖለቲከኞች እንዳማራጭ እያቀረቡ እንደሆነ ያመለክታሉ። በአባይ ወንዝ ላይ ኢትዮጵያ ለመስራት ያቀደችዉ ግድብ የዉሃዉን ፍሰት ያዛባ እንደሆነ ለማጥናት ከአንድ ዓመት በላይ እንደፈጀ የተገለፀዉ የገለልተኛ ባለሙያዎች መድረክ አባይ ላይ የሚሠራዉ ሥራ የዉሃዉ ፍሰት ላይ ይህ ነዉ የሚባል ተፅዕኖ አይፈጥርም ሲል መደምደሙ ተነግሯል። የተፋሰሱ ሃገራት ኢትዮጵያ፤ ሱዳንና ግብፅ በአባልነት እንደሚገኙበት በተነገረዉ በዚህ የባለሙያዎች መድረክ ድምዳሜ ያልረካች የምትመስለዉ ግብፅ ፖለቲከኞች ከፕሬዝደንት ሙሐመድ ሙርሲ ጋ ያካሄዱት ዉይይት ድንገት በመገናኛ ብዙሃን ቀጥታ መቅረቡም ፖለቲከኞቹ የግድቡን ስራ ለማስቆም የሰነዘሯቸዉን አስተያየቶች ለአየር አብቅቷል።

Blauer Nil Wasserfall Äthiopien
ምስል DW/Azeb Tadesse Hahn

ኢትዮጵያም በፋንታዋ የፖለቲከኞቹ ሃሳብ «የቀን ቅዠት» መሆኑን በመጠቆም በጀመረችዉ ሥራ እንደምትቀጥል አመልክታለች። የሁለቱ ሃገራት የቃላት ጦርነት ወዴት አቅጣጫ ያመራል ተብሎ መገመት ይቻላል። በደቡብ አፍሪቃ የዓለም ዓቀፍ የጸጥታ ጥናት ተቋም የፖለቲካ ተንታኝ አንድርዉስ አታ አሳሞዋ ጉዳዩ ከሁለቱም ወገን ጥንቃቄ ያሻዋል ይላሉ፤

«በእኔ አመለካከት ይህ ጉዳይ በጥንቃቄ ዘመናችን በሚጠይቀዉ መልኩ ለዉይይት ቀርቦ መፍትሄ ካልተፈለገለት ወደፊት ችግር እንደሚኖር የሚያመላክት የማስጠንቀቂያ ደወል ነዉ። ይህ ስለወደፊቱ ነዉ የሚናገረዉ። በተጨማሪም የቃላት ልዉዉጡ፤ ሰሞኑን በቴሌቪዢን ግብፅ እንዴት ያለ አማራጭ ልትወስድ እንደምትችል የታየዉ ጉዳዩን ለመፍታት የዲፕሎማሲ አማራጭ መጠቀምን ያመላክታል ብዬ አስባለሁ። ምን እንኳን ይህ በሁለቱ ሃገሮች መካከል ዉጥረቱን ያባብሳል ቢባልም እና ከግብጽ ወገን የመጣዉ ሃሳብ ለዚህ ጉዳይ የተሻለ አማራጭ እንዲፈልጉ ኢትዮጵያዉያንንም ሆነ ግብፆችን የሚያቅፍ እንደሚሆን ነዉ የማስበዉ።»

ዛሬ የወጡ ዘገባዎች የግንባታዉ ተግባር የዉሃዉን ፍሰት የሚጎዳ ከሆነ ግብፅ ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ የጀመረችዉን የግድብ ግንባታ ለማስቆም አማራጮች ክፍት ናቸዉ ማለቷን አመልክተዋል። ይህ ምናልባት ሁለቱን ሃገሮች ወደጦርነት አቅጣጫ ይመራል ማለት ይቻል ይሆን? ተንታኙ ይህ አንዱ አማራጭ ቢመስልም የመጨረሻዉ ሊሆን እንደሚችል ነዉ የሚገምቱት፤

«ይህ ከጉዳዩ ሙሉ ለሙሉ ዉጪ ነዉ ማለት አይቻልም አንዱ አማራጭ ይመስለኛል። ሆኖም ግን የሁለትዮሽ ድርድሮች ሁሉ ካልተሳኩ የመጨረሻዉ አማራጭ የሚሆን ነዉ የሚመስለኝ። ሁለቱም ወገኖች ለፍጥጫም ሆነ ለጦርነት ይጣደፋሉ ብዬ አላስብም። ቀደም ብዬ እንደገለፅኩት ሁኔታዉ ሁለቱ ወገኖች የጋራ መፍትሄ እንዲፈልጉ የሚያስገድድ ነዉ። ግብፅ ከኢትዮጵያ ጋ ጦርነት ለመግጠም ትቻኮላለች ብዬ አላስብም ኢትዮጵያም ወደጦርነት መግባት የምትፈልግ አይመስለኝም። ከሁለቱም ወገን የተካረረዉ ሁኔታ እንዲነጋገሩ ያቀራርባቸዋል ብዬ አስባለሁ።»

Der veschmutzte Nile
አባይ ካይሮ ላይምስል Nael Eltoukhy

የአባይ ዉሃ ለግብፅ የሞትና ህይወት ጉዳይ መሆኑን አድርዉስ አታ አሳሞዋ ከሁለቱ ሃገሮች ጦርነት ግን ማንም እንደማያተርፍ አጽንኦት ሰጥተዋል። የተፋሰሱ ሃገሮች ቀደም ሲል የተስማሙበትን ስምምነትም ግብፅ ከልቧ የተቀበለችዉ እንደማይመስላቸዉም አመልክተዋል። በአንፃሩ የግብፅና የኢትዮጵያ መንግስታት ይህን የአባይን ጉዳይ ከፍ ያደረጉት በወቅቱ በየበኩላቸዉ በአገር ዉስጥ የገጠማቸዉን የፖለቲካ ጫና ለማስተንፈስ ነዉ የሚሉ ወገኖች አሉ። አሳሞዋም ይህም አንዱ ሊሆን ይችላል ባይናቸዉ፤

«የሁለቱንም ሃገሮች የዉስጥ ፖለቲካ ጉዳዮች ስትመለከቺ በከፊል እዉነት ሊሆን ይችላል። ሆኖም ግን ጉዳዩ ወዴት እንደሚያመለክት በተለይም ግብፅ ሁሉም አማራጮች ክፍት ናቸዉ ማለቷን ስትመለከች፤ የማቀጣጠል ባህሪዉን ና ወዴት እንደሚሄድ ስታይዉ፤ ከአገር ዉስጥ ፍላጎት ያለፈ ነገር መኖሩንና የየአገራቱን ብሄራዊ ፍላጎት የማስጠበቅ ነገር ያመላክታል። እናም እነዚህ ሁሉ እንዳሉበት እስማማለሁ። ሆኖም ግን ቀደም ብዬ እንዳልኩት ልንጠነቀቀዉ የሚገባንን ጉዳይ የሚያመለክት ቅድመ ማስጠንቀቂያ ነዉ።»

ከሁለቱ ወገኖች የቃላት ዉርዉራ በተጓዳኝ በግብፅ የኢትዮጵያ ኤምባሲ በመሳሪያ መከበቡን፤ እዚያም የሚኖሩ ኢትዮጵያዉን ወከባ እንደደረሰባቸዉ፤ ከየመኖሪያቸዉም መዉጣት እንዳልቻሉ ተጠቅሶ የኢንተርኔት ዘገባ ቀርቧል። ይህን ለማጣራት ወደስፍራዉ ደዉለን ያነጋገርናቸዉ በካይሮ የኢትዮጵያ ኤምባሲ የሚኒስቴር አማካሪ አቶ በላይ ግርማይ ኤምባሲዉ መደበኛ ተግባሩን እያከናወነ እንደሚገኝ ነዉ የገለፁልን።

ሸዋዬ ለገሠ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ