1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በሳውዲ አረቢያ የኢትዮጵያውያን ስቃይ

ረቡዕ፣ ኅዳር 4 2006

ሳዉድ አረቢያ የሚገኙ ኢትዮጵያዉያን ዛሬም የድረሱልን ድምጻቸዉን እያሰሙ ነዉ። የሀገሪቱ መንግስት ላለፉት ወራት ሰጥቶ የቆየዉ የምህረት ቀነገደብ ካለፈ ወዲህ በዜጎችና የጸጥታ ኃይሎች ይፈጸምብናል የሚሉት በደልም ገደብ ማለፉን ይናገራሉ።

https://p.dw.com/p/1AGiB
Foreign workers wait for a taxi as they leave the Manfuhah neighbourhood of the Saudi capital Riyadh on November 10, 2013, after two people have been killed in clashes between Saudi and other foreign residents the previous day, according to the Saudi police. On November 4, the authorities began rounding up thousands of illegal foreign workers following the expiry of a final amnesty for them to formalise their status. AFP PHOTO/FAYEZ NURELDINE (Photo credit should read FAYEZ NURELDINE/AFP/Getty Images)
ምስል AFP/Getty Images

በሕጋዊ የመኖሪያ ፈቃድ ከ24ዓመታት በላይ እዚያ እንደኖሩ ለዶቼ ቬለ የገለጹት አንድ ዜጋ ደግሞ ኢትዮጵያዉያኑ ላይ ሀገሬ የሚያሳየዉ ጥላቻ ዛሬ አልተጀመረም ባይናቸዉ። ከያሉበት ታፍሰዉ በመጠለያ ስፍራ እንደተሰበሰቡ ያመለከቱ ወገኖች ደግሞ ኤምባሲዉ አልደረሰልንም፤ ካለንበት የሚያወጣን አጣን ይላሉ።

ከእነልጆቻቸዉ ታፍሰዉ መጠለያ ከተከተቱ እናቶች አንዷ ናቸዉ። እንባቸዉን እየታገሉ የሚሉት አንድ ነገር ነዉ፤ ድሃም ብትሆን ሀገር አለን። ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት በርካቶች በአዉቶብስ ያለ ሕጋዊ መኖሪያ ፈቃድ ሀገሪቱ ዉስጥ የተገኙትን የተለያዩ ሀገር ዜጎች በመሰብሰብ ወደመጠለያ ስፍራ ያጓጉዛሉ። በስልክ ያነጋገርኳቸዉ ኢትዮጵያዉያን የት ቦታ እንዳሉ ማወቅ እንደተሳናቸዉ ቢናገሩም ወንዶችና ሴቶችን ለየብቻ ተደርገዉ በመጠለያ መታጎራቸዉን ገልጸዉልኛል። ሴቶቹ ሶስት ሺህ እንሞላለን ባዮች ናቸዉ። ይህንም በአንድ አካባቢ ብቻ መሆኑ ነዉ። እዚህ ቦታ ካሉት አንዷ እሷ ብቻ ሳትሆን ሌሎችም በተሰባሰቡበት መጠለያ ስፍራ ባለዉ መጥፎ ሽታ ምክንያት ድምፃቸዉ መዘጋቱን ለበሽታም መዳረጋቸዉን ገልጻልኛለች። ወንዶች ትላለች ወጣቷ ከአረብ ወጣቶች ጋ ጸብ ዉስጥ ገብተዋል። እንደእሷ ገለጻም ሸባቦቹ ግራ የተጋቡትን ኢትዮጵያን ሴቶች ባገኙበት አስገድደዉ ይደፍራሉ፤ ከመጠለያዉም አፍነዉ ይወስዳሉ።

Foreign workers hold their passports as they gather outside a labour office, after missing a deadline to correct their visa status, in Riyadh November 4, 2013. The streets of the Saudi capital Riyadh were unusually quiet on Monday as many expatriates stayed at home to avoid the start of a government crackdown on illegal foreign workers. REUTERS/Faisal Al Nasser (SAUDI ARABIA - Tags: POLITICS BUSINESS EMPLOYMENT SOCIETY IMMIGRATION)
ምስል Reuters/Faisal Al Nasser

ወደሳዉዲ ከተሻገረ ብዙም ወራት እንዳልሆነዉ የገለፀልኝ ከስልጤ ነዉ የመጣሁት ያለኝ ሽፋ ሸምሱ ደግሞ ወደሀገሩ ለመመለስ ተዘጋጅቷል፤ ግን ወደአዉሮፕላን ማረፊያ ይወስዳችኋል የተባለዉን አዉቶብስ መጠበቅ ቀጥሏል የተባለዉ ግን የለም ይላል።

ሳዉዲ ዉስጥ ኢትዮጵያዉያን ብቻ ሳይሆን በርካታ የዉጭ ዜጎች በሠራተኝነት ይገኛሉ። መንግስት ሕጋዊ የመኖሪያ ፈቃድ ለሌላቸዉ በሰጠዉ የምህረት ጊዜ የተጠቀሙ የባንግላዴሽ፤ ፊሊፒንስ፤ ህንድ፤ ኔፓል፤ ፓኪስታንና የመን ዜጎች ቁጥር በርካታ መሆኑን ዘገባዎች ያመለክታሉ። እንደአዣንስ ፍራንስ ፕረስ ዘገባ ከሆነም ወደአንድ ሚሊዮን ገደማ የሚሆኑ ተጠሪ የሚሆኗቸዉ ቀጣሪዎች አግኝተዋል። ዘጋቢዎች ያነጋገሯቸዉ ኢትዮጵያን ግን ለዓመታት ያፈሩትን ንብረት በርካሽ ለመሸጥ ተገደዋል ገሚሱንም ለሰዎች ሰጥተዋል። በእጅ የቋጠሯትን ገንዘብም መኖሪያ ፈቃድ ለማስተካከል በደላልነት ለቀረቧቸዉ የሳዉዲ ብልጣብልጦች አጉርሰዋል። ተስፋ ያደረጉትን ግን አላገኙም።

በሺዎች የሚቆጠሩ አፍሪቃዉያን ስደተኞች በሳዉዲ መንግስት ኃይሎች ታስሰዉ ቢያዙም የኃይል ጥቃቱ የበረታዉ ኢትዮጵያዉያኑ ላይ ነዉ ይላሉ እዚያ የሚገኙት ወገኖች።

ሳዉዲ የሚገኙ ወገኖች ዛሬም ኤምባሲዉ ላይ የሚያቀርቡት ቅሬታና ለመንግስትም የሚያቀርቡትን አቤቱታ በማስመልከት ከዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ምላሽ ለማግኘት ያደረግነዉ ተደጋጋሚ ሙከራ ባለመሳካቱ የባለስልጣናቱን ሃሳብ ማካተት አልቻልንም።

Zum Thema - Zwei Tote bei Krawallen illegaler Einwanderer in Saudi-Arabien
ምስል Reuters/Faisal Al Nasser

ከሃገሪቱ መውጣት ያልቻሉ ዜጎች በዋና ከተማይቱ በሪያድና በሌሎችም ከተሞች በጎዳናዎች ላይ እየወጡ መንግሥት በአስቸኳይ ወደ ሃገራችው እንዲልካቸው ሲጠይቁ ከየአካባቢዎቹ ነዋሪዎች ጋር መጋጨታቸውን የጂዳው ወኪላችን ነብዩ ሲራክ ዘግቧል ።
በርካታ ኢትዮጵያውያን ዛሬም ሳውዲ አረቢያ ውስጥ በመሰቃየት ላይ መሆናቸውን እየተናገሩ ነው ። እነዚሁ ከሃገሪቱ መውጣት ያልቻሉ ዜጎች በዋና ከተማይቱ በሪያድና በሌሎችም ከተሞች በጎዳናዎች ላይ እየወጡ መንግሥት በአስቸኳይ ወደ ሃገራችው እንዲልካቸው ሲጠይቁ ከየአካባቢዎቹ ነዋሪዎች ጋር መጋጨታቸውን የጂዳው ወኪላችን ነብዩ ሲራክ ዘግቧል ። ሳውዲ አረቢያ ውስጥ ያለህጋዊ የስራና የመኖሪያ ፈቃድ የሚኖሩ የውጭ ዜጎች ህጋዊ ሰነድ እንዲያወጡ አለያም ወደ ሃገራቸው እንዲመለሱ መንግሥት የሰጠው የምህረት ቀነ ገደብ ካበቃ ዛሬ 10ኛ ቀኑን ይዟል ። በነዚህ 10 ቀናት ውስጥ ወደ 23 ሺህ የሚጠጉ ኢትዮጵያውያን ለሳውዲ መንግሥት እጃቸውን መስጠታቸው ተዘግቧል ። የጂዳውን ወኪላችንን ነበዩ ሲራክን ስለ አጠቃላዩ ሁኔታ በስልክ አነጋግሬዋለሁ ።

ሸዋዬ ለገሠ / ነበዩ ሲራክ
ሂሩት መለሰ
አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ