1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የተፈናቃዮች ቅሬታ

ቅዳሜ፣ ግንቦት 10 2016

“... ህፃናት በዛፍ ስር ነው ያሉት፣ ከብቶቻቸውም ተዘርፈዋል፣ ተፈናቃዮቹ ወደ 10 ሺህ ይደርሳሉ፣ ምንም እርዳታ አልቀረበም፣ መንግስት እስካሁን ምላሽ አልሰጠም፣ ከእሁድ እለት ጀምሮ የተደረገ ድጋፍ ምንም የለም፣ አሁን ግጭቱ ቆሟል፣ አንፃራዊ ሰላም በአካባቢው ይታያል፡፡”

https://p.dw.com/p/4g1oz
Äthiopien | Straßenszene in Gambela
ምስል Negassa Desalegn/DW

የጋምቤላ ተፈናቃዮች ዕርዳታ አልደረሰንም አሉ

ባለፈው ሳምንት እሁድና ሰኞ በጋምቤላ ክልል ኢታንግ ልዩ ወረዳ በነበረ ግጭት ከቀያቸው የተፈናቀሉ ሰዎች እርዳታ እንዳላገኙና ህፃናትንና እናቶችን ጨምሮ በየዛፉ ስር መቀመጣቸውን ነው አስተያየታቸውን ለዶቼ ቬሌ የተናገሩ ተፈናቃዮች የገለፁት፡፡

ስማቸው እንዳይጠቀስ ፈለጉ አንድ አስተያየት ሰጪ የሚከተለውን ብለዋል፡፡

“...ህዝብ በሙሉ  መኮድ የሚባለውን መንደር ለቅቆ ማለት ነው፣ ማሮልና ባዜል ወደሚባል ቦታ ነው ያለው፣ ህፃናት በዛፍ ስር ነው ያሉት፣ ከብቶቻቸውም ተዘርፈዋል፣ ተፈናቃዮቹ ወደ 10 ሺህ ይደርሳሉ፣ ምንም እርዳታ አልቀረበም፣ መንግስት እስካሁን ምላሽ አልሰጠም፣ ከእሁድ እለት ጀምሮ የተደረገ ድጋፍ ምንም የለም፣  አሁን ግጭቱ ቆሟል፣ አንፃራዊ ሰላም በአካባቢው ይታያል፡፡” ነው ያሉት፡፡

ሌላ አስተያየትሰጪ ደግሞ ተፈናቃዮቹ ዘመድ ከሚሰጣቸው የእለት ምግብ ውጪ የደረሰላቸው አካል የለም ብለዋል፡፡

አንድ የኢታንግ ወረዳ ነዋሪም ለተፈናቃዮቹ አስቸኳይ እርዳታ ባለመቅረቡ በችግር ላይ እንደሆኑ ጠቁመዋል፣ መንግስት ለችግሩ አፋጣኝ ምላሽ አልሰተም ሲሉም ወቅሰዋል፡፡

“... እስካሁን እርዳታ አልደረሰላቸውም፣ የክልሉ አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ቢሮ ኃላፊ እርደታ እየፈላለግን ነው ቢሉም እስካሁን የመጣ ነገር የለም፣ መንግስት ጥረት እያደረገ አይደለም፡፡” ሲሉ ከስሰዋል፡፡

የጋምቤላ ከተማ በከፊል
የጋምቤላ ከተማ በከፊልምስል Privat

የጋምቤላ ክልል አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ቢሮ ኃላፊ አቶ ጋድቤል ሙን በነበረው ግጭት ከ11ሺህ በላይ ሰዎች መፈናቀላቸውንና በሶስት የተለያዩ አካባቢዎች እንደሰፈሩ አመልክተዋል፣ ሁኔታውም ከባድ እንደሆነ ነው ስረዱት፡፡

“11 ሺህ 370 ሰዎች ተፈናቅለዋል፣ ተፈናቃዮቹም ዶሮንግ፣ ባዜልና ኢታንግ ኪር በሚባሉ አካባቢዎች ተጠልለዋል፣ ሁኔታው ከባድ ነው፣ዝናብ ሲጥል ይቸገራሉ፣ ባገኘነው መረጃ መሰረት በቅርብ እርዳታ እንዲደርሳቸው ይደረጋል፡፡” ብለዋል፡፡

የጉዳቱን መጠን የሚያሳይ ሪፖርት እንደደረሳቸው ጠቁመው ያን መሰረት በማድረግ እርዳታ እንዲቀርብላቸው ጥረት ይደረጋል ነው ያሉት፡፡

ከዚህ በፊትም በጋምቤላ ክልል በጆር ወረዳ በነበረ ግጭት በተመሳሳይ በርካቶች መፈናቀላቸውንና የእለት ድጋፍ ሲጠይቁ እንደነበር መዘገባችን ይታወሳል፡፡

ዓለምነው መኮንን

ዮሃንስ ገብረእግዚአብሄር